mandag 31. mars 2014

የማሕበረ ቅዱሳን የመጨረሻዎቹ ቀናት – ከተመስገን ደሳለኝ


በኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም የሚመራው መንግስት ከናቅፋ እስከ ጉና ተራራ ያሉ ምሽጎቻቸውን ከሰማይ በጦር አይሮፕላን፣ ከምድር እሳት በሚያዘንቡ ቢ.ኤሞችና መድፎች ሳያቋርጥ ደበድብም፤ በሀገሪቱ ሰሜናዊ አካባቢ ከቀን ወደ ቀን ግዛታቸውን እያሰፉ የተጠናከሩት ‹‹ወንበዴዎች›› ራስ ምታት ሆነውበታል፡፡ የኤርትራ ‹‹ነጻ አውጪ›› ቤዝ-አምባው በተወሰነ መልኩም ቢሆን ለጥቃት የመጋለጥ እድሉ አናሳ በሆነው የሳህል በረሃ በመሆኑ አብዛኛው የአመራር አባል መሸሸጊያው አድርጎታል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በትግራይ አካባቢ የሚንቀሳቀሱት የወያኔ መሪዎች ምሽጋቸው እንደ ሳህል ምቹ ባለመሆኑ፤ በርካታ ክፉ ቀናትን ያሳለፉት በተራራማ አካባቢዎች በሚገኙ የኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ገዳማት ውስጥ ተደብቀው እንደሆነና ከቦታ ቦታ መዘዋወር ሲፈልጉም የመነኮሳቱን አልባሳት ይጠቀሙ እንደነበረ በትግሉ ዙሪያ የተዘጋጁ ድርሳናት ያወሳሉ፡፡ በተለይም ታጋይ መለስ ዜናዊ፣ አባይ ፀሀዬ፣ ግደይ ዘርአፅዮን፣ ስዩም መስፍን፣ ስብሐት ነጋን…. የመሳሰሉ የአመራር አባላት የገዳማቱ ቤተኛ ነበሩ፡፡ ከዚሁ ጋ ተያይዞ የሚነገርም አንድ ታሪክ አለ፤ የመንግስት ፀጥታ ሰራተኞች ሁለት የ‹‹ወንበዴ›› መሪዎች በትግራይ በሚገኝ አንድ ገዳም ውስጥ ከመነኮሳቱ ጋር ተመሳስለው መሸሸጋቸው መረጃ ይደርሳቸውና በጥቂት ሰዓታት ውስጥ እስከ አፍንጫቸው የታጠቁ ወታደሮችን በመላክ ዙሪያ ከበባ ያደርጋሉ፡፡ ይሁንና መደበቂያ በመስጠት የረዷቸው መነኮሳት ሁለቱን ታጋዮች ‹‹ወይባ›› በመባል የሚታወቀውን ረጅሙን ቀሚሳቸውን አልብሰው እና ቆብ አስደፍተው ከአካባቢው በማሸሽ ይታደጉዋቸዋል፡፡ የታሪኩ ባለቤት መለስ ዜናዊ እና አባይ ፀሀዬ ነበሩ፡፡ በርግጥ እነዚህ የ‹‹ወንበዴ›› መሪዎች ‹በእንዲህ አይነቱ ከመርፌ አይን እጅግ በጠበበ ዕድል ህይወታችን ከሞት መንጋጋ ተርፎ ኮለኔል መንግሥቱን በጓሮ በር ወደ ዜምባብዌ ሸኝተን በትረ-መንግሥቱን ለመጨበጥና ለሃያ ምናምን ዓመታት ኢትዮጵያን ታህል ታላቅ ሀገር አንቀጥቅጠን ለመግዛት እንበቃለን› የሚል ጠንካራ እምነትና የእርግጠኝነት ስሜት በወቅቱ ነበራቸው ብሎ ማሰብ ለእነርሱም ቢሆን እጅግ አዳጋች ይመስለኛል፤ የሆነው ግን ይህ ነበር፡፡

‹‹ማሕበረ-ቅዱሳን››


መለስ ዜናዊና ጓዶቹ በለስ ቀንቷቸው ባልጠበቁት ፍጥነት የመንግሥት ‹‹ጠንካራ ይዞታ›› የሚባሉ ከተሞችን ሳይቀር እየተቆጣጠሩ ወደ አዲስ አበባ የሚያደርጉትን ግስጋሴ ሲያፋጥኑ፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ደግሞ በመንግሥቱ ኃይለማርያም ሰብሳቢበት፣ በደህንነት ሠራተኞች እና የኢሠፓ ካድሬዎች ገፋፊነት ትምህርታቸውን አቋርጠው ለወታደራዊ ስልጠና ደቡብ ኢትዮጵያ ወደሚገኘው ብላቴና የጦር ማሰልጠኛ ከተቱ፤ ዩኒቨርሲቲውም ተዘጋ፡፡

…ከመላው ዘማቾቹ አስራ ሁለት የሚሆኑ ተማሪዎች ተሰባስበው ሲያበቁ፣ በየቀኑ ካምፓቸው አቅራቢያ ወደሚገኘው ‹ሚካኤል ቤተ-ክርስቲያን› በመሄድ፣ ከመዓቱ ይታደጋቸው ዘንድ ፈጣሪያቸውን በፀሎት መማፀን የህይወታቸው አካል አደረጉት፤ ከቀናት በኋላም በአንዱ ዕለት አንድም ለመታሰቢያና ለበረከት፣ ሁለትም ስብስቡ ሳይበተን ወደፊት እንዲቀጥል በሚል ዕሳቤ ‹ማህበረ ሚካኤል› ብለው የሰየሙትን የፅዋ ማህበር መሠረቱ፡፡ …ይሁንና ከመካከላቸው አንዳቸውም እንኳ በ1977 ዓ.ም በ‹ፓዊ መተከል› ዞን የተደረገውን ‹የመልሶ ማቋቋም› ፕሮግራም እንዲያመቻቹ በዘመቱ ተማሪዎች ከተመሠረተውና ከተለያዩ የፅዋ ማህበራት ጋር በመዋሀድ የዛሬውን ‹ማህበረ-ቅዱሳን› እንደሚፈጥሩ መገመት የሚችሉበት የነብይነት ፀጋ አልነበራቸውም፤ የሆነው ግን እንዲያ ነበር፡፡

ኃይማኖትን ጠቅልሎ የመያዝ ዕቅድ

በትጥቅ ትግሉ ወቅት የህወሓት አመራር ገዳማትን ለመሸሸጊያነት ብቻ ሳይሆን ለእርካብ መወጣጫነትም ጭምር ተጠቅሞባቸዋል፡፡ ከድርጅቱ መስራቾች አንዱ የነበረው አረጋዊ በርሄ ለዶክትሬት ዲግሪ ማሟያ ‹‹A Political History of the Tigray People’s Liberation Front (1975-1991): Revolt, Ideology and Mobilisation in Ethiopi›› በሚል ርዕስ ጽፎት፤ ኋላም ወደ መጽሐፍ በቀየረው የጥናት ጽሁፉ ላይ፣ ‹‹የቤተ-ክርስቲያኗን ሥልጣን (በትግራይ የነበረውን) ለማድቀቅ ሲባል በስብሀት ነጋ የሚመራ የስለላ ቡድን ተቋቋመ፡፡ ይህ ቡድንም ደብረ-ዳሞን ጨምሮ በትግራይ ውስጥ ባሉ ገዳማት አባላቱን መነኮሳት በማስመሰል፣ የገዳማቱን እንቅስቃሴ በህወሓት ፍላጎት ስር የማስገዛት ስራ ሰርቷል›› ሲል በገፅ 317 ላይ ገልጿል፡፡ ድርጅቱ ሙሉ በሙሉ ሐይማኖትን ጠቅልሎ ለመያዝ የተነሳበትን ገፊ-ምክንያትም እንዲህ በማለት አብራርቶታል፡-

‹‹ቤተ-ክርስቲያኗ ተከታዮቿን፣ ለነበረው የኢትዮጵያ መንግስት እንዲገዙ ከማስተማር በዘለለ የብሔራዊ ንቃት (ማንነት) ማስተማሪያም ነበረች፡፡ …ለህወሓት እንቅስቃሴ እንቅፋት እንደነበረች ግልፅ ነው፡፡ ስለዚህም ቤተ-ክርስቲያኒቱን በህወሓት ዓላማ ስር ለማሳደር ፍላጎት ነበር፤ በዚህ የተነሳም የእርሷን ተፅእኖ ለማግለል ጥልቅ እርምጃዎች ተወስደዋል፡፡›› (ገፅ 315-316) ዶ/ር አረጋዊ ‹‹ጥልቅ እርምጃዎች›› ብሎ ከጠቀሳቸው መካከል አንደኛው ‹‹ለአጥቢያ ቀሳውስቱ ኮንፍረንስ በማዘጋጀት፣ በትግራይ ውስጥ ያሉትን ቤተ-ክርስቲያናት ለብቻ ነጥሎ ህወሓት በሚያራምደው የትግራይ ብሔርተኝነት ስር ማካተት›› እንደነበረ በዚሁ መጽሐፍ ጠቅሷል፡፡ ይሁንና አስገምጋሚ መብረቅ የወረደብን ያህል የምንደነግጠው፣ ዶ/ሩ ከዚሁ ጋ አያይዞ ‹‹የተጨቆነው የትግራይ ብሔርተኝነት የተነሳሳውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያንን ተፅእኖ ለመገዳደር ነው›› በማለት መመስከሩን ስናነብ ነው፡፡ የአረጋዊ መረጃ የሰሚ-ሰሚ ወይም በቢሆን ሃሳብ የተቀኘ አይደለም፤ ይልቁንም ራሱም በመሪነትና ሃሳብ በማዋጣት ከተሳተፈበት ከድርጅቱ የፖለቲካ ፕሮግራም የተቀዳ እንጂ፡፡

የሆነው ሆኖ ህወሓት ከ1970-72 ዓ.ም ድረስ ባሰለጠናቸው ካድሬ ‹‹ካህናት›› አማካኝነት ‹‹ነፃ በወጡ›› መሬቶች ላይ ራሱን የቻለ የቤተ-ክህነት አስተዳደር (ከሲኖዶሱ የተገነጠለ) መመስረቱ ይታወሳል፡፡ ድርጅቱ ለእነዚህ ቤተ-ክርስቲያናት መተዳደሪያ ደንብ ከመቅረፅ አልፎ ዓላማውንም እንደ አስርቱ ትዕዛዛት በፍፁም ልባቸው የተቀበሉ ‹‹መንፈሳዊ ክንፍ›› አድርጓቸው እንደነበረ፣ አረጋዊ በርሄ ተንትኖ አስረድቷል፡፡ እንዲህ አይነቱ ሰርጎ ገብነት በእስልምናም ላይ መተግበሩ አይዘነጋም፡፡ በተለይም የእምነቱ ተከታዮች በሚበዙበት አካባቢዎች ወላጆቻቸው ሙስሊም የሆኑ ታጋዮችን እየመረጠ እና ከክርስቲያን ቤተሰብ የወጡ ካድሬዎችንም ሀሰተኛ የሙስሊም ስም እየሰጠ ‹የትግሉ ዓላማ እስልምናን ማስፋፋት› እንደሆነ በመግለፅ የፕሮፓጋንዳ ስራ ይሰራ ነበር፡፡ በዚህ ስልቱ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የአንዳንድ ዓረብ ሀገራትን ቀልብ ማግኘት ችሏል፡፡ ይህ ደግሞ ከዓረቦች በገፍ ዕርዳታ ያጎረፈለት ሲሆን፣ ወደ መሀል ሀገር የሚያደርገውን ጉዞም አፋጥኖለታል፡፡

ከመንግስት ለውጥ በኋላም ሁለቱን ሐይማኖቶች የተቆጣጠረው በታጋይ ‹‹ካህናት›› እና ‹‹ሼሆች›› ለመሆኑ በርካታ ማሳያዎች አሉ፡፡ ዛሬም በኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት የበላይ በሆነው ጠቅላይ ቤተ-ክህነት ውስጥ ከሚገኙት አስራ ስምንት መምሪያዎች፣ አስራ ስድስቱ በህወሓት ሰዎች የመያዛቸው ኩነት ስልቱ በተሳካ ሁኔታ መተግበሩን ያስረግጣል፡፡ በተለይ ዋነኛው ሰው አቡነ ማቲያስ ሲኖዶሱን ብቻ በሚመለከት ጉዳይ ላይ ጭምር ውሳኔ ከመተላለፉ በፊት ‹‹የመንግስት ባለሥልጣናትን ላማክር›› ሲሉ በተደጋጋሚ መደመጣቸው እና አንዳንድ ጳጳሳት ተቃውሞ በሰነዘሩባቸው ቁጥር በአፃፋው ‹‹መንግስት ያግዘኛል ብዬ ነው እዚህ መንበር ላይ የተቀመጥኩት፤ ባያግዘኝ ሥልጣኑን አልቀበልም ነበር›› በማለት በግላጭ ሲመልሱ መስተዋላቸው ለስርዓቱ ጣልቃ-ገብነት እንደማሳያ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ከዚህ ቀደም ለሶስት ወር የቋሚ ሲኖዶሱ አባል ሆነው የሰሩ አንድ ጳጳስም ‹‹ሁልጊዜም ቋሚ ሲኖዶሱ ሲሰበሰብ እርሳቸው (ፓትርያርኩ) ‹መንግስት እንዲህ አለ›፣ ‹መንግስት ሳይፈቅድ›… የሚል ንግግር ይጠቀማሉ›› በማለት ለፋክት አስተያየት ሰጥተዋል (በነገራችን ላይ ፓትርያርኩ የመዘንጋት፣ ለውሳኔ የመቸገር፣ እንቅልፍ የማብዛትና መሰል ችግሮች ስራቸውን እያስተጓጎሉባቸው እንደሆነ ይነገራል፤ ራሳቸውም ‹‹ሲጨንቀኝ እተኛለሁ፤ ስተኛ ደግሞ እረሰዋለሁ›› በማለት ችግሩን አምነው ተቀብለዋል)

በእስልምና እምነት ውስጥም የመንግስት ጣልቃ-ገብነት ከቀድሞውም መጅሊስ የባሰ እንደሆነ በርካታ መዕምናን የሚያውቁት እውነታ ነው፡፡ ይህ መጅሊስ የሚዘወረው እንደተለመደው በምክትል ፕሬዚዳንቶች ሲሆን፤ ይች አይነቷ ጨዋታ ደግሞ ህወሓት ጥርሱን የነቀለበት ስለመሆኑ ነጋሪ አያሻም፡፡ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ሼህ ከድር ለ17 ዓመታት የትግራይ ክልል መጅሊስና የሸሪአ ፍ/ቤቱን ደርበው በመያዝ መእምናኑን ቀጥቅጠው ሲገዙ ከመቆየታቸውም በላይ ታጋይ እንደነበሩ በኩራት ለመናገር የሚደፍሩ እንደሆነ የቅርብ ሰዎቻቸው ይመሰክራሉ፡፡ በአናቱም ከታማኝ የመረጃ ምንጭ ባይረጋገጥም የመጅሊሱ ፕሬዚዳንት ሼህ ኪያር መሀመድ ከእኚሁ ‹‹ታጋይ›› ምክትላቸው ጋር በአንዳንድ ጉዳዮች መስማማት ባለመቻላቸው እና ‹‹መንግስት የሚያዘውን ሁሉ ለመስራት ለምን እንገደዳለን?›› የሚል ተቃውሞ እስከማሰማት በመድረሳቸው በቅርቡ ከኃላፊነታቸው ሊነሱ እንደሚችሉ ተወርቷል፡፡

ኢህአዴግ እና ‹‹መንፈሳዊ›› ገበያው


ግንባሩ የእምነት ተቋማትን በአብዮታዊ ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ጠርንፎ መያዝን እንደ ዋነኛ ዓላማ አድርጎ የመንቀሳቀሱ መግፍኤን ከሶስት ጉዳዮች አንፃር በአዲስ መስመር ለመተንተን እሞክራለሁ፡-
የመጀመሪያው ቤተ-ክህነት በነገስታቶቹ ዘመን የነበራትን ፖለቲካዊ ተሰሚነት (ምንም እንኳን ራሱ ኢህአዴግም በአፋዊነት ከማውገዝ ቸል ባይልም) ለቅቡልነት መጠቀሚያ የማድረግ ፍላጎቱ ነው፡፡ በገቢር እንደታየውም በኃይል በተቆጣጠራቸውም ሆነ ካድሬዎቹ ሊደርሱባቸው በማይችሉ የገጠር ቀበሌዎች ተቀባይነት ለማግኘት ማህበራዊ አክብሮት ባላቸው ሼሆች፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት… ሲቀሰቅስ ተደጋጋሚ ጊዜ ተስተውሏል፡፡ እንዲሁም የእስልምና እምነት በታሪክ ያሳለፈውን አገዛዛዊ ጭቆናንም ሆነ የደርጉን ሁሉንም ሐይማኖት ማግለልን በማጎን ለፕሮፓጋንዳ ተጠቅሞበታል (በወቅቱ የድርጅቱ አመራር አባል የነበረው አቶ ገብሩ አስራት፣ እንደ ሼሆች በመልበስና በመጠምጠም ከፍተኛ አስተዋፆ ማበርከቱን ብዙሀኑ ታጋዮች አይዘነጉትም) በዚህ ዘመንም በቤተ-እምነቶች ካድሬ-ጳጳሳትንና ካድሬ-n ሼሆችን አሰርጎ የማስገባቱ ምስጢር ይኸው ነው፡፡

በሁለተኛነት እንደምክንያት ሊጠቀስ የሚችለው የታገለለትን ዘውግ ተኮር ፖለቲካ ያለአንዳች ተግዳሮት ማሳለጥን ታሳቢ ማድረጉ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም የሁሉም ሐይማኖቶች ‹‹የሰው ልጅ በሙሉ የአንድ አምላክ ፍጡሮች ናቸው›› በሚል አስተምህሮ የሚመሩ ከመሆናቸው አኳያ፣ በዘውግ ከፋፍሎ ማስተዳደርን ቀላል አያደርገውምና ነው፡፡ ስለዚህም መፍትሔው አክራሪ ብሔርተኛ ‹‹መንፈሳውያን›› በየእምነት ተቋማቱ እንዲፈለፈሉ እና ከፍተኛውን የሥልጣን እርከን መቆጣጠር እንዲችሉ በማብቃት ላይ የተመሰረተ ብቻ መሆኑን የህወሓት መሪዎች ያውቃሉ፡፡ ይህ ‹‹እውቀታቸው››ም ይመስለኛል ሀገራዊ ስሜት የሌላቸው፣ በችሎታ ማነስ እና በስነ-ምግባር ጉድለት የሚታወቁ፤ እንዲሁም በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ ቅቡል ያልሆኑ ሰዎች ቦታውን እንዲይዙ እስከማድረግ ያደረሳቸው፡፡

የራሳቸው የስለላ መዋቅርም በጥቅምት 2 ቀን 1995 ዓ.ም ‹‹ለዋናው መ/ቤት፣ አዲስ አበባ፤ ከ-ል.ዮ፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስን ጉዳይ ይመለከታል›› በሚል ርዕስ ለደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት በላከው ጥናታዊ ዘገባ ላይ እውነታውን እንዲህ ሲል ገልፆታል፡- ‹‹…ለፓትርያርኩ ወዳጅነት አላቸው የሚባሉ ሊቃነ ጳጳሳት ከሦስትና አራት ብዙም ያልበለጡ ናቸው፡፡ ፓትርያርኩ ምንም ዓይነት ተቀባይነትና ከበሬታ ያጡ በመሆናቸው ህልውናቸውን የአንዳንድ መሪዎችን ስም በመጥራትና እንደማስፈራሪያ በመጠቀም ላይ የተንጠላጠለ ሆኗል››፡፡ ከዚህ ሪፖርት በኋላም እንኳ ለማስተካከል አለመሞከሩ መከራከሪያውን አምነን እንድንቀበል ያስገድደናል፡፡

አገዛዙ መንፈሳዊ ተቋማትን ጠቅልሎ ለመያዝ ለሚያደርገው እንቅስቃሴ በሶስተኛነት ሊጠቀስ የሚችለው ምክንያት፣ ምንም እንኳ ‹‹ተሳክቷል›› ሊባል ባይቻልም፤ በስነ-ምግባር መታነፅ፣ በሀገር አንድነት ማመን፣ ለሕዝብ ጥቅም መቆም፣ የትኛውንም ህገ-ወጥነት ‹ለምን› ብሎ መጠየቅና መሰል መንፈሳዊ አስተምህሮዎችን መርሁ አድርጎ የሚነሳ ትውልድ እንዳይፈጠር መከላከልን ታሳቢ በማድረግ እየሰራ ያለውን ሴራ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ምክንያቱም የስርዓቱ ሰዎች በዚህ መልኩ የሚቀረፅ ትውልድን ዛሬ ባነበሩት አይነት የጭቆና ቀንበር ለተራዘሙ ዓመታት መግዛት ከባድ እንደሆነ ለመረዳት አይሳናቸውምና ነው፡፡ ከዚሁ ጋር አንስተን ማለፍ ያለብን ጭብጥ፤ መቃብር ከሚቆፈርለት የኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነት ጋር የሚያያዝ ነው፤ የሐይማኖቱና የማዕከላዊ መንግስቱ የቅድመ-አብዮቱ ጋብቻ (በምንም አይነት መከራከሪያ ትክክለኛነቱን ልንሟገትለት ባንችልም)፣ ቤተ-ክርስቲያኗ ለኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነቱ የታሪክ ብያኔ ከፍተኛ አስተዋፆ ማድረጓን አያስክደንም፡፡ ይህም ‹የሐይማኖቱን ተቋም የብሔርተኝነቱ ወካይ ሆኖ እንዲታሰብ ይገፋዋል› ብሎ ለሚያምነው ህወሓት፣ ሐይማኖቱ ተቋማዊ ነፃነት እንዳይኖረው የሚቻለውን ሁሉ ሲያደርግ፤ ሐይማኖቱን በማዳከም የብሔርተኝነት መንፈሱንም ማላላት ይቻላል ከሚል መነሾ ነው ብሎ መደምደም ተምኔታዊ አያስብልም፡፡

ገደል አፋፍ የቆመው ማሕበረ ቅዱሳን…


ስርዓቱ የሐይማኖት ተቋማትንና መንፈሳዊ መሪዎቹን ለመቆጣጠር ገፊ-ምክንያቶች ሆነውታል ብዬ ከላይ ለማብራራት የሞከርኳቸውን ሶስት ምክንያቶች ሙሉ ለሙሉ መተግበርን አስቸጋሪ ያደረገበት፣ ቀጥታ በምዕምናኑ የተመሰረቱ ማሕበራት መሆናቸውን መገመት ይቻላል፡፡ ለማስረጃም ያህል ከኦርቶዶክስ ክርስትና-ማሕበረ ቅዱሳን፤ ከእስልምና ያለፉትን ሁለት ዓመታት የእምነቱ ተከታዮች ወካይ ሆኖ የተመረጠው ኮሚቴ አባላት መንግስትንም ሆነ መጅሊሱን በመገዳደር ያደረጉትን አበርክቶ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይሁንና የሙስሊሙን ተወካዮች በገፍ ሰብስቦ እስር ቤት ካጎረ በኋላ፣ ከሲኖዶሱም ሆነ መሰል ማሕበራት ጠንካራ እንደሆነ የሚነገርለትን ማሕበረ ቅዱሳንን ዋነኛ ኢላማው አድርጎ ለመደፍጠጥ የቆረጠ ይመስላል፡፡ የማሕበሩ አባላት በዓለማዊ እውቀት የተራቀቁ፣ በሀገር አንድነት በፍፁም የማይደራደሩ፣ በጥቅመኝነት የማይደለሉ… የመሆናቸው ጉዳይ አገዛዙ ከኃይል አማራጭ የቀለለ መፍትሔ የለም ብሎ እንዲያምን አድርጎታል ብዬ እገምታለሁ፡፡

በርግጥ በአቶ መለስ ዜናዊ ይዘጋጅ እንደነበረ ከህልፈቱ በኋላ በተነገረለት የኢህአዴግ የንድፈ ሃሳብ መጽሔት ‹‹አዲስ ራዕይ›› ከተወሰኑ ዓመታት በፊት አብዛኛውን ጊዜ ‹‹የከሰሩ ፖለቲከኞች ‹ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ናት፣ አንድ ሐይማኖት አንድ ሀገር› እና ‹ሙስሊሙ ማሕበረሰብ ቀደም ሲል ሲደርስበት የነበረውን በደል በማራገብና በመቀስቀስ፤ ከዚህም አልፎ ተገቢነት የሌላቸው አዳዲስ ጥያቄዎችን በማቅረብ ለማነሳሳትና ለማተረማመስ ሲሰሩ ማየት የተለመደ ሆኗል›› በማለት ከሚያቀርበው የሾላ-በድፍን ፍረጃ ዘልሎ ብዙም መንፈሳዊ ማሕበራትን በስም ጠቅሶ ሲያወግዝ አይሰማም ነበር፡፡ ዛሬ ዛሬ ግን ማንኛውንም ሐይማኖታዊ የመብት ጥያቄን ‹‹ወሃቢያም ይሁን ማሕበረ ቅዱሳን…›› በማለት ማውገዙ የተለመደ ሆኗል፡፡ ከውግዘትም ተሻግሮ ጥያቄያቸውን በሕጋዊ መንገድ ወደ አደባባይ ያወጡትን የሙስሊሙን ተወካዮች ሰብስቦ አስሯል፤ በተለያየ ጊዜ የተደረጉ ሰላማዊ ተቃውሞዎችንም በማስታከክ በበርካታ የእምነቱ ተከታዮች ላይ ግድያና ስቀየትን ጨምሮ ብዙ ግፍ በመፈፀም ጉዳዩን በጠብ-መንጃ ብቻ የሚፈታ አድርጎ ካወሳሰበው ሰነባብቷል፡፡

‹‹ቀጣዩ የኢህአዴግ ኢላማ ማሕበረ ቅዱሳን ይሆን?›› በሚል ርዕስ ከስድስት ወር በፊት በዚሁ መጽሔት ላይ ለማተት እንደሞከርኩት ሁሉ፤ ከላይ በተዘረዘሩ የፖለቲካ አጀንዳዎች እና በሚቀጥለው ዓመት የሚካሄደውን አገር አቀፍ ምርጫ በለመደው የማጭበርበር መንገድ አሸንፎ ያለኮሽታ የሥልጣን እድሜውን ለማራዘም ዓለማዊም ሆነ መንፈሳዊ ነፃ ተቋማት እንዳይኖሩ በይፋ ኢ-ሕገ መንግስታዊ ድርጊቶችን እየፈፀመ ያለው የእነ አባይ-በረከት መንግስት፣ በአሁኑ ወቅት ሙሉ ትኩረቱን ማሕበረ ቅዱሳን ላይ ማድረጉን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ይህንን አፈና ለማሳካትም ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በፍፁም ልባቸው ከመተባበር ለአፍታም እንደማያመነቱ በርካታ ማሳያዎች አሉ፡፡
ለምሳሌ ያህልም አንዱን በአዲስ መስመር ላቅርብ፡-

ከወራት በፊት የአዲስ አበባ ሀገረ-ስብከት አስተዳደርን ወደ ዘመናዊነት ለማሻገር ሲኖዶሱ ጥናት ተደርጎ እንዲቀርብለት ውሳኔ አሳልፎ ነበር፡፡ እናም ጥናቱ ተጠናቆ ይፋ መደረጉን ተከትሎ ከአንዳንድ የደብር አስተዳዳሪዎች ብርቱ ተቃውሞ ስለገጠመው፣ በሀገረ-ስብከቱ ሥራ-አስኪያጅ አቡነ እስጢፋኖስ አማካኝነት በጠቅላይ ቤተ-ክህነት አዳራሽ ከሁሉም አድባራትና ገዳማት የተወጣጡ 2700 ሰዎች የሚሳተፉበትና አስራ አራት ቀን የሚፈጅ የውይይት ፕሮግራም ይዘጋጃል፡፡ ይሁንና ውይይቱ በተጀመረ በሁለተኛው ቀን ጠዋት ፓትርያርኩ፣ ከአቡነ እስጢፋኖስ ጋር በስልክ ከሞላ ጎደል እንደሚከተለው መወዛገባቸውን ሰምቻለሁ፡-

‹‹ጥናቱን የሚሰሩት ባለሙያዎች ናቸው ብለውኝ አልነበረም ወይ?››
‹‹አዎ! ታዲያስ ባለሙያዎች ናቸው የሰሩት፡፡››
‹‹አይደለም! የማሕበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው፤ እርስዎ አታለውኛል!››
‹‹የጥናት ኮሚቴው አባላት በቤተ-ክርስቲያን ልጅነታቸውና በየአጥቢያው ባላቸው ተሳትፎ ተጠርተው የመጡ ሙያቸውን ‹አስራት› ያደረጉ ናቸው፡፡››
‹‹በፍፁም! ጥናቱ የማሕበረ ቅዱሳን ነው!››
‹‹ቅዱስ አባታችን ቢሆንስ? ከጠቀመን ችግሩ ምንድን ነው?››
‹‹በቃ! ውይይቱ ከመንግስት ይቋረጥ ተብሏል፡፡››
‹‹ለምን ይቋረጣል?››
‹‹የጥናቱ ተቃዋሚዎች ረብሻ ያስነሳሉና የፀጥታ ስጋት አለ፡፡››
‹‹ለምንድን ነው ረብሻ የሚያስነሱት? ከፈለጉ መጥተው መሳተፍ ይችላሉ፤ እኛ እየተወያየን አይደለም እንዴ! ተቃውሞ ያለው መጥቶ ሃሳቡን ይግለፅ እንጂ ማቋረጥ እንዴት መፍትሄ ይሆናል? ደግሞስ ሲኖዶሱ አይደለም ወይ ‹ሰነዱ ወደታች ወርዶ ይተችበት› ብሎ የወሰነው?››
‹‹የለም! ይቁም ተብሏል፤ ይቁም!››
‹‹እንግዲያውስ የከለከለው አካል ራሱ መጥቶ ይንገረን፡፡››

…የስልክ ምልልሱ ከተጠናቀቀ ከሰዓታት በኋላ አንድ ባለሥልጣን አቡነ እስጢፋኖስ ቢሮ ድረስ መጥቶ ትእዛዙን ያስተላለፈው እርሱ እንደሆነ ገልፆ ውይይቱ እንዲቋረጥ አሳሰባቸው፤ እርሳቸውም ‹‹እናቋርጣለን፤ ነገር ግን እናንተ ‹የፀጥታ ስጋት አለ› ብላችሁ በደብዳቤ ኃላፊነቱን ውሰዱ፡፡ እኛም ለካህናቱም ሆነ ለመዕምናኑ ሁኔታውን ዘርዝረን እንገልፃለን›› የሚል ምላሽ ሰጥተው ይሸኙታል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ ለጊዜው ግልፅ ባልሆነ አንድ ምክንያት መንግስት ‹‹ይቋረጥ›› የሚለውን ማስፈራሪያ ሊያነሳ የቻለው፡፡ ኩነቱ ግን ፓትርያርኩ ማሕበሩን በጥርጣሬ ማየታቸውንና አገዛዙ ለሚወስድበት ማንኛውም አይነት እርምጃ ተባባሪ መሆናቸውን የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡

ሌላው መንግስትና ፓትርያርኩ፣ ማሕበረ ቅዱሳንን ለማፍረስ በሰምና ወርቅነት እየሰሩ መሆናቸውን የሚያመላክተው የዛሬ ሳምንት በጠቅላይ ቤተ-ክህነት የማሕበሩ ተቃዋሚዎች ያደረጉትን ውይይትና የአቋም መግለጫ ስናስተውል ነው፡፡ ለመጽሔቱ ዝግጅት ክፍል የደረሰው በድምፅ የተቀረፀ የውይይቱ ሙሉ ክፍል እንደሚያስረዳው፣ ተሰብሳቢዎቹ ማሕበሩን በተመለከተ ባወጡት የአቋም መግለጫ የሚከተሉትን ነጥቦች ዘርዝረዋል፡- ‹‹የዋነኛ አመራሮቹ የባንክ አካውንት ይመርመር፣ የማሕበሩ ሒሳብ መንግስት በሚመድበው የውጪ ኦዲተር ይመርመር፣ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረቶቹ (ከቀረጥ ነፃ ያስገባቸው ቀላልና ከባድ መኪናዎቹ ሳይቀሩ) ወደ ቤተ-ክህነት ይግቡ፣ የንግድ ተቋማቱ (ትምህርት ቤት፣ ሬስቶራንቶቹን፣ ንዋየ ቅድሳት ማምረቻና ማከፋፈያውን) ያስረክብ፣ ከምዕምናን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚቀበለው አስራት እየፈረጠመበት ስለሆነ እንዳይቀበል ይከልከል፣ የግቢ ጉባኤ (በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት) እርሱ በሚቀርፀው እንዳይወሰዱ መስራት፣ ተጠሪነቱ ከዋና ሥራ-አስኪያጁ ተነስቶ፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ ስር አንዱ ንዑስ ክፍል ይሁን…›› የሚሉና የመሳሰሉት ይገኙበታል፡፡

ከዚህ ሴራ ጀርባ ፓትርያርኩና መንግስት በትብብር መቆማቸውን የሚያሳየው በተቀረፀው ድምፅ ላይ፣ የውይይቱ መሪ አዳራሹን መጠቀም የቻሉት በአቡኑ መልካም ፍቃድ እንደሆነና እርሳቸው በዛሬው ውይይት ያልተገኙት የሕዳሴው ግድብ ምክር ቤት አባል በመሆናቸው ግዮን ሆቴል ስብሰባ ስላለባቸው መሆኑን ከመግለፅም በዘለለ፤ ‹‹ቅዱስ አባታችን በዚህ የተቃውሞ ምክንያት ከሥራ የሚባረር የለም አይዟችሁ አትፍሩ ብለውናል›› በማለት ሲናገሩ መደመጣቸው ነው፡፡ በተጨማሪም ‹‹ከዚህ ግቢ አቅም ኖሮት የሚያስወጣን የለም፤ ካስወጡን ግን መንግስታችን ስለሚተባበረን (ቸር ስለሆነ) ከእርሱ ሌላ መሬት ተቀብለን የራሳችንን ቤተ-ክርስቲያን እናቋቁማለን›› እና ‹‹የኦርቶዶክስ እምነት አገልጋዮች የሚል ማሕበር እንመሰርታለን›› እስከማለት መድረሳቸው ከአገዛዙ ጋር ያላቸውን የጠበቀ ቁርኝት ያመላክታል፡፡ በነገራችን ላይ በስብሰባው እንዲሳተፉ ከተጠሩት ከመቶ ስልሳ ዘጠኙ አድባራትና ገዳማት፣ እንዲሁም ከ10 ሺህ በላይ ሠራተኞቻቸው መካከል የተገኙት የስምንት አድባራት አስተዳዳሪዎችና 150 ሠራተኞች ብቻ እንደነበሩ ከመረጃ ምንጮቼ አረጋግጫለሁ፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ በተለይም በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ምኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማሪያም አዝማችነት ማሕበሩ ላይ የደቦ ዘመቻ ከተከፈተ ሰነባብቷል፡፡ በተከታታይ በ‹‹ጥናት›› ስም የሚወጡ ወረቀቶች ማሕበሩን ከአክራሪነትም አሻግረው ‹‹የግንቦት ሰባት መንፈሳዊ ክንፍ›› ሲሉ ይወነጅሉታል፡፡ በጥቅሉ የእነዚህ ‹‹ጥናት›› ተብዬዎች መደምደሚያ ‹‹ማሕበሩ የትምክተኞች ምሽግ ነው፣ አክራሪነት አለበት፣ አመራሩና የሕትመት ውጤቶቹ የፖለቲካ አዝማሚያ ይታይባቸዋል፣ በቤተ-ክርስቲያን አስተዳደር ጣልቃ ይገባል፣ ሕዝቡ በመንግስት ላይ አመኔታ እንዳይኖረው ይሰራል፣ በውጭ ፅንፈኛ የፖለቲካ ኃይሎች ይዘወራል›› የሚሉ ናቸው፡፡ የማሕበሩ የአመራር አባላት እንዲህ አይነቱን ውንጀላ በተመለከተ በተለያየ ጊዜ ከአቶ በረከት ስምኦን እስከ ዶ/ር ሽፈራው ተክለማሪያም፤ ከአዲስ አበባ የፀጥታ ኃላፊዎች እስከ ጠቅላይ ሚንስትሩ የደህንነት አማካሪ ፀጋዬ በርሄ ድረስ ያሉ ባለሥልጣናትን በቢሮአቸው ተገኝተው ውንጀላው ማስረጃ የማይቀርበበት የሀሰት እንደሆነ ቢያስረዱም መፍትሄ እንዳላገኙ ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በግልባጩ በመንግስት ተቋማት ያሉ የፋክት መረጃ አቀባዮች፣ በግንቦት ወር ከሚካሄደው የሲኖዶሱ መደበኛ ጉባኤ በፊት፣ ከሃያ የሚበልጡ የማህበሩ አመራርን ከሽብርተኝነት ጋር በማያያዝ ለመክሰስ እና ማሕበሩንም እንደተለመደው በዶክመንተሪ ፊልም ለመወንጀል ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ከሶስት ሳምንት በፊት በአቡነ ገብርኤል ሰብሳቢነት የሚመራው የሐይማኖቶች ምክር ቤት ስብሰባውን ካጠናቀቀ በኋላ ዶ/ር ሽፈራው አቡኑን ቃል-በቃል የጠየቃቸው ጥያቄም ይህንን መረጃ የሚያጠናክር ነው፡-

‹‹በማሕበረ ቅዱሳን አመራር ውስጥ ከሃያ በላይ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት አሉ››
‹‹ለዚህ ምንድን ነው ማስረጃህ? አቅርበውና እስቲ እንየው?››
‹‹ሀገር ውስጥ ካሉ ፅንፈኛ ጋዜጠኞች በተጨማሪ በስደት የሚገኙና በሽብር ተግባር የተሰማሩ ጋዜጠኞች በአመራርነት አሉበት (የሁለት ሰዎችን ስም ጠቅሷል)››
‹‹እኛ እስከምናውቀው ማሕበሩ ከእንዲህ አይነት ተግባር የራቀ ነው፤ እናንተ ማስረጃ አለን ካላችሁ ደግሞ አቅርቡልንና እንየው፤ ከዚህ ውጪ ይህንን አይነት ክስ አንቀበልም፡፡››

በአናቱም ከወራት በፊት የስርዓቱ የንድፈ ሃሳብ መጽሔት የማሕበሩን ስም ሳይጠቅስ በደፈናው የወነጀለበትን እና ‹‹ለምን?›› ብለው የሚጠይቁ ጳጳሳትን በሚከተለው አገላለፅ ማሸማቀቁን ስናስታውስ የማሕበሩ ዕጣ-ፈንታ በመጨረሻዎቹ ቀናት ላይ መቆሙን ያስረግጥልናል፡፡

‹‹በኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን ውስጥ ትርምስና ብጥብጥ ለመፍጠር፤ በኦርቶዶክሶችና ሌሎች ሐይማኖቶች መካከል ግጭት ለመቀስቀስ የሚሞክሩት የደርግና የተለያዩ ትምክህተኛ ኃይሎች ቅሪቶች ናቸው፡፡ እነዚህ የትምክህት ኃይሎችና አንዳንድ የእምነቱ አባቶች በጋራ ሐይማኖትን በፖለቲካ ዓላማ ዙሪያ መጠቀሚያ አድርገው እየሰሩ ለመሆናቸው ከ97 ምርጫ በኋላ እንዳንድ በአሜሪካ የሚገኙ ጳጳሳት ቅንጅት በጠራው ሰልፍ ላይ የሐይማኖት አባትነት ካባቸውን እንደለበሱ ከመሰለፍ አልፈው አስተባባሪ ሆነው መታየታቸው በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡›› (አዲስ ራዕይ ሐምሌ-ነሐሴ 2005)

የሆነው ሆኖ ከፍረጃውና ከእስራቱ በተጨማሪ ማሕበሩን ለማዳከም በዋናነት በአገዛዙ የተነደፉት እቅዶች ማሕበሩ መሰረቱን የጣለበት የግቢ ጉባኤን ከመከልከልና ንብረቶቹን ከመውረስ ጋር የሚያያዙ ናቸው (ከላይ የተጠቀሰው የአቋም መግለጫም ለማሕበሩ የደም-ስር የሆኑትን እነዚህን ሁለት ጉዳዮች ትኩረት እንደሰጣቸው ልብ ይሏል)

ስቅለትን-ለተቃውሞ


ኢህአዴግ ወደ ስልጣነ-መንበሩ ከመጣ ሦስተኛ ዓመት ላይ ‹‹የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ግቦችና ቀጣይ እርምጃዎች›› በሚል ርዕስ ለካድሬዎቹ በበተነው ድርሳን (በሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ የተዘጋጀ ነው ተብሎ ይገመታል)፤ ይህን አሁን የተነጋገርንበትን ሐይማኖታዊ ተቋማትን በሚያቅዳቸው የስልጣን ማራዘሚያ አማራጮች ስለመጠቀም ካወሳ በኋላ ተቋማቱን ለስርዓቱ ፖሊሲዎች እንዲታመኑ ማድረጉ ዋነኛ እንደሆነ ያሰምርበታል፡፡ ይህ የማይቻል ከሆነ ደግሞ፣ እስከ ከፍተኞቹ መንፈሳዊያን መምህራን ድረስ ዘልቆ በመግባት ሐይማኖቶቹን መምራት የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ግብ መሆን እንዳለበት ያው ሰነድ በግልፅ ቋንቋ ይናገራል፡፡ እንግዲህ ከመጅሊሱ እስከ ማሕበረ ቅዱሳን ያየነው መንግስታዊ አፈና የዚህን ሃያ ዓመት የሞላው የተፃፈ ሀሳብ መተግበርን ነው፡፡

ግና፣ ከዚህ ቀደም በተፃፈ ነውረኛ ሀሳብ ትግበራ ፊት ከሁለት አስርት በላይ ህልውናውን ለማቆየት የተጋው ማሕበረ ቅዱሳን፣ ከላይ በሚገባ በጠቀስኳቸው አሳማኝ መረጃዎች እና ተጨባጭ ሁነቶች በተከታታይ መከሰት መጨረሻው ምዕራፍ ላይ እንደደረሰ ተመልክተናል፡፡ በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ደግሞ፤ መነሳት የሚኖርበት መሰረታዊ ጥያቄ፣ እንዴት ይህን ማሕበር ወደ ቀጣዩ ትውልድ ማሻገር ይቻላል? የሚለው ሲሆን፤ ምላሾቹም ሁለት ናቸው፡፡ የመጀመሪያው የማሕበሩ አመራሮችና አባላት እስከዚህች ቀን እያደረጉ ያለው የውስጥ ለውስጥ የእርምት እንቅስቃሴን ይመለከታል፡፡ በሐይማኖቱ ተቋማት በኩል ለዓመታት ሲሞከር የቆየው ይኸኛው አማራጭ፣ እንደ አስተዋልነው ማሕበሩን ሞት አፋፍ ላይ ከመድረስ ሊታደገው አልቻለም፡፡ ስለዚህም፣ ወደ ሁለተኛውና ዋነኛ የመፍትሔ አማራጭ መሻገር ግድ የሚል ይመስለኛል፡፡ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ርዕሰ-ጉዳይ ላይ ስፅፍ ለማስረዳት እንደሞከርኩት፤ የማሕበሩ አመራሮች፣ አባላት እና ደጋፊዎች ወደ አደባባይ በመውጣት፤ ማሕበራቸውን ብቻ ሳይሆን ህልውናቸውንና ህያውነታቸውን የመሰረቱበትን ሐይማኖት ለማውደም የሚተጋውን ስርዓት በሰላማዊ አመፅ መናድ ብቸኛው የዚህ አስቸጋሪ ጊዜ መሻገሪያ መንገድ ነው፡፡ በዋናነት የተማሩ ከተሜ ወጣቶችን፣ በአለማዊም ሆነ በትምህርተ-ሐይማኖቱ የማይታሙ ዜጎችን የያዘው ይህ ማሕበር፤ ከህዝበ ሙስሊሙ ‹‹ድምፃችን ይሰማ›› የአደባባይ ተቃውሞ ስኬቶችና ሂደቶች በመማር፤ ፊቱ በተገተረው ኢህአዴግ ላይ በሕጋዊና ሰላማዊ እምቢተኝነት ከማመጽ የተሻለ አማራጭ እንደማይኖረው የሚረዳ ይመስለኛል፡፡

‹‹ችግሮች ሁሉ የየራሳቸው በጎ ገፆች አሏቸው›› እንዲሉ፤ ማሕበሩ የደረሰበት ይህ ፈታኝ ጊዜን ተከትለው የሚመጡ ሁለት ወቅቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው፣ በቀጣዩ ወር የሚካሄደው የስቅለት በዓል ነው፡፡ የሐይማኖቱ ተከታዮች በሙሉ በየቤተ-ክርስቲያናቱ የሚውሉበት ይህ በዓል፣ አገዛዙ እጁን ከማህበሩ ላይ እንዲያነሳ ለመጠየቅ የተመቸ ቀን ስለመሆኑ ማስታወስ አባላቱን አሳንሶ መገመት እንደማይሆን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ሁለተኛውና በእጅጉ የተሻለ ነው ብዬ የማስበው ጊዜ ደግሞ ቀጣዩ የ2007 ምርጫን ነው፡፡ ለየትኞቹም የህገ-መንግስቱ ሀሳቦች አልያም የሞራል ዕሴቶች የማይገዛው ኢህአዴግ፣ በሐይማኖቱ ላይም ሆነ በማሕበሩ ላይ የዘረጋውን የረከሰ እጅ እንዲያነሳ ያለው ብቸኛ አማራጭ ሕዝባዊ አመፅ መሆኑ ላይ እስከተማመንን ድረስ፣ ከዓመታዊ የንግስ በዓላት ጀምሮ ያሉ መድረኮችን በዕቅድ ለመጠቀም የዝግጅቱ ጊዜ ዛሬ ነው፡፡ ይህ አይነቱ የተቃውሞ እንቅስቃሴም፣ ካነሳነው ርዕሰ-ጉዳይ አኳያ የማሕበሩን መኖር የሚሹ ሁሉ ቀጣዩን የምርጫ ወቅት ለማስገደጃነት የመጠቀም ተሞክሮዎቻቸውን ተፈላጊው ብቃት ላይ እንደሚያደርሰው አምናለሁ፡፡ ጥቂት ሊባሉ የማይችሉ አባላቱ፣ የምርጫውን ተጨባጭ ዕድል መንግስታዊ ተቋማት በማሽመድመድ ጭምር እንዴት ስርዓቱን ወደመቃብሩ ማሻገር እንደሚያውቁ ስንገነዘብ፤ ቀሪው ጉዳይ ‹‹ሐይማኖታችሁን ተከላከሉ›› ብለው ላስተማሩት ቅዱሳን መጻሕፍትና ለሰማያዊው መንግስት የመታመን ብቻ እንደሚሆን እንረዳለን፡፡

torsdag 27. mars 2014

ዓባይና የአሜሪካ ጨዋታ (ፕ/መስፍን ወልደ ማርያም)

አሥራ ዘጠነኛው ምዕተ-ዓመት አስተሳሰብ ከዚህ ቀጥሎ የተጠቀሰው ዓላማ ለአውሮፓ ቄሣራውያን ዋና ግባቸው ሆኖ እስከሃያኛው ምዕተ-ዓመት ዘልቆአል፤ አሀን ፈጽሞ በተለየ ዘመን አሜሪካ ይህንን አስተሳሰብ ይዞ የተነሣ ይመስላል።
ኢትዮጵያን የተቆጣጠረ ዓባይን ይቆጣጠራል፤ ዓባይን የተቆጣጠረ ግብጽን ይቆጣጠራል፤ ግብጽን የተቆጣጠረ ኃይልቀይ ባሕርን ከመግቢያና መውጫው 
ጋር ይቆጣጠራል፤ቀይ ባሕርን ከመግቢያና መውጫው ጋር የተቆጣጠረ ኃይልዓለምን ይቆጣጠራል።
አሜሪካ በግብጽ ላይ የተከለው ጥፍሩ ሲነቃነቅ መነቀሉ አለመቅረቱን ስላወቀው ሌላ የሚተክልበት አገር ይፈልጋል፤ በአካባቢው የግብጽን ነፍስ የሚነካ ከኢትዮጵያ የተሻለ አገር የለም፤ ለአሜሪካ ዓለም-አቀፍ ዓላማ ኢትዮጵያ ስትመረጥ የአሁኑ የመጀመሪያው አይደለም፤ በመሀከለኛው ምሥራቅ የአረቦችን የተባበረ ኃይል ለመቋቋም የተመረጡ ሦስት አረብ ያልሆኑ አገሮች — ቱርክ፣ ኢትዮጵያና ፋርስ (ኢራን) — ነበሩ፤ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የአሜሪካ ዓለም-አቀፍ ኃይል መሰማት በጀመረበት ጊዜ ኢትዮጵያን ከከበቡአት የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ጋር የነበርዋትን የቆዩ ውዝግቦች ለመቋቋም የአሜሪካ ድጋፍ በጣም አስፈላጊ ነበር፤ አሜሪካን ከአውሮፓ አገሮች ጋር እየመዘኑና እያመዛዘኑ የኢትዮጵያን ጥቅም ለማስከበር የተደረገው ዲፕሎማሲ (ዓለም-አቀፍ የሰላም ትግል) የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን መንግሥት በእውነት ከሚያኮሩት ተግባሮች አንዱ ነው፤ ይህንን ትግል አምባሳደር ዘውዴ ረታ ምስጋና ይድረሰውና የኤርትራ ጉዳይ በሚለው መጽሐፉ ግሩም አድርጎ አሳይቶናል።
ምናልባት ገና ያልተጠና ጉዳይ በዘመኑ ኢትዮጵያ የነበራት ታሪካዊ ክብር ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ታሪክና ዝና ጋር ተዳምሮ በአፍሪካ ተደማጭነት ነበራት፤ ይህንን ኢትዮጵያ በአፍሪካ አገሮች ላይ የነበራትን ጫና (የዛሬውን አያርገውና) በመጠቀም አሜሪካ አፍሪካን በሙሉ ለዓላማዋ ለማሰለፍ ኢትዮጵያን መሣሪያዋ ለማድረግ ትሞክር ነበር።
እየቆየ የኢትዮጵያ መንግሥት የነጻነት መንፈስን በማሳየት ለአሽከርነት አልመች በማለቱና ለአሜሪካም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች (የእውቀት ጥበቦች) በመፈጠራቸው ኢትዮጵያ ለአሜሪካ ዓለም-አቀፍ ዓላማ አስፈላጊነትዋ በመቀነሱ አሜሪካ ኢትዮጵያን ችላ ማለት ጀመረ፤ የ1966 ግርግር ከዚህ ጋር ተያይዞ የመጣ መሆኑን ጠለቅ ብሎ ማጥናት ያስፈልጋል፤ በዚህ መሀልም የሶቭየት ኅብረት ዓለም-አቀፋዊ ጉልበት እየተሰማ በመሄዱ አሜሪካ በኢትዮጵያ ላይ የነበረውን ዓላማ ቀስ በቀስ እየለወጠ ሄደ፤ ከዚህም ጋር የሶቭየት ኅብረት ተጽእኖ እያደገ ሄደ፤ የአሜሪካ አያያዝ እየላላ ሲሄድ የሶቭየት ኅብረት አያያዝ እየጠበቀ ሄደ፤ 1966 የአሜሪካ መውጫና የሶቭየት መግቢያ ሆነ ለማለት ይቻል ይሆናል፤ ከዚሁ ጋር አብሮ የሚታየው በኢትዮጵያ የባህላዊው ሥርዓት መሰነጣጠቅና የቆየው ትውልድ መዳከም ነው፤ የአሜሪካ መዳከም ሶቭየት ኅብረትን ሲያጠነክር፣ የአሮጌው ትውልድ መዳከም አዲሱን ትውልድ አጠነከረ፤ ይህ ማለት አሮጌው ትውልድ ከአሜሪካ ጋር የተያያዘውን ያህል አዲሱ ትውልድ ከሶቭየት ኅብረት ጋር ተያያዘ፤ የኢትዮጵያ የውስጥ ሁኔታ ብቻውን ለውጥ እንዳላመጣና ዓለም-አቀፍ ሁኔታዎችና የልዕለ ኃያላኑ ተጽእኖም ምን ያህል እንደነበረ አመላካች ነው።
የአጼ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት መውደቅና የአሜሪካ ተጽእኖ መዳከም በአንድ በኩል፣ የደርግ መፈጠርና የእነኢሕአፓና መኢሶን በአጋፋሪነት መውጣት ከሶቭየት ኅብረት ተጽእኖ መጠናከር ጋር በሌላ በኩል በኢትዮጵያ ውስጥ አዲስ ሁኔታን ፈጠሩ፤ የአዲሱን ሁኔታ አዲስነት በግልጽና በትክክል መገንዘብ ያስፈልጋል፤ በኢትዮጵያ ለብዙ ሺህ ዓመታት ተከብሮና ታፍሮ የቆየው የዘውድ ሥርዓት ተናደ፤ ተዋረደ፤ በኢትዮጵያ ስር እየሰደዱ የነበሩ መሳፍንትና መኳንንት ከስራቸው ተመነገሉ፤ አዲስ የመሬት አዋጅ ወጣና የመሬት ከበርቴዎችን ሙልጭ አውጥቶ ገበሬውን በሙሉ እኩል ባለመሬት አደረገው፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻ ወጣ ባይባልም የኢትዮጵያ መሬት ነጻ ወጣ፤ ወታደር፣ ገዢ ሰላማዊው ሕዝብ ተገዢ ሆነ፤ ትርፍ መሬትና ትርፍ ቤት ሁሉ ተወረሰ፤ ቤትን የሚያከራዩ የኪራይ ቤቶችና ቀበሌዎች ብቻ ሆኑ፤ ደሀዎችንና መሀከለኛ ገቢ ያላቸውን ሰዎች ኑሮ ለማቃለል ከሦስት መቶ ብር በታች የነበረው የቤት ኪራይ ሁሉ ተቀነሰ፤ ደርግ በሁለት ዓመታት ውስጥ የአብዛኛውን ገበሬ ኑሮና የአብዛኛውን የከተማ ነዋሪ ኑሮ የሚነኩ መሠረታዊ ለውጦችን አወጀ፤ እያደር ደርግ አስከፊ እየሆነና እየተጠላ ቢሄድም እነዚህ ሁለት አዋጆች ብዙ ኢትዮጵያውያንን እስከዛሬ ድረስ ለደርግ ባለውለታ አድርገዋል፤ እነዚህ አዋጆች ወያኔ ገና አፍርሶ ያልጨረሳቸው የደርግ ሐውልቶች ናቸው።
በውጭ አመራር ደግሞ የአሜሪካ ተጽእኖ ክፉኛ ተበጠሰ፤ አሜሪካ ማለት ስድብና ውርደት ሆነ፤ አሜሪካ ማለት በዝባዥነትና የቄሣራዊ ተልእኮ አራማጅ ማለት ሆነ፤ የአሜሪካ ማስታወቂያ ቢሮ ተዘጋ፤ ብዙ የአሜሪካ እንደወባ መከላከያ ያሉ የተራድኦ ድርጅቶች ተዘጉ፤ አሜሪካ ለዩኒቨርሲቲዎች ሲያደርግ የነበረውን እርዳታ አቋረጠ፤ በዚህ በተለይም የዓለማያ ዩኒቨርሲቲ በጣም ተጎዳ፤ የወባ ቢምቢም ከ‹‹ኢምፒሪያሊዝም›› ጭቆና ነጻ ወጣችና  አዲስ አበባ ደረሰች! ይባስ ብሎም አለማያ ዩኒቨርሲቲ ያፈራቸው አሉ የተባሉት በተለያዩ የእርሻ ሙያዎች የተካኑት አብዛኞች ሙልጭ ብለው ከአገር ወጡ።
አሜሪካ ከደርግ ጋር እየተጋገዘ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ክፉኛ አዳከመው፤ አያይዞም በኢትዮጵያ ዳር ዳር የሚነደውን እሳት አቀጣጠለው፤ በአንድ በኩል የውስጥ ተገንጣይ ቡድኖችን — የትግራይ ነጻ አውጪ ድርጅት፣ የኤርትራ ነጻ አውጪ ድርጅት፤ የኦሮሞ ነጻ አውጪ ድርጅት — በሌላ በኩል በድንበርም ሆነ በሌላ ምክንያት ከኢትዮጵያ ጋር የሚፋለሙትን አገሮች ሶማልያንና ሱዳንን በግልጽ መርዳት ጀመረ፤ እንዲያውም ከግብጹ ፕሬዚደንት ሳዳት ጋር እየተመካከረ ኢትዮጵያን ለማዳከም ሞከረ፤ ከመሞከርም አልፎ ኤርትራን አስገነጠለ፤ የኢትዮጵያን ዙፋን ለወያኔ አመቻቸ፤ አሜሪካ ኮሚዩኒስት ነኝ የሚለውን ወያኔን በጎሣ ፖሊቲካ አስታጥቆ ቀለቡን እየሰፈረ በኢትዮጵያ ላይ ሠራው፤ ደርግ በሰይፍ ብቻ አንድነትን ለማምጣት መሞከሩና ሕዝቡን ለጦርነት ማነሣሣቱ አሜሪካንን አስደንግጦታል፤ ለአሜሪካ ደርግ የቀሰቀሰው የአንድነት ብሔራዊ ስሜት የኢትዮጵያን ድንበር አልፎ የሚፈስስ መስሎ ታየው፤ በዚህም ምክንያት የኢትዮጵያን የአንድነት ብሔራዊ ስሜት የማፈራረስ እቅዱን አወጣ፤ የሚያሳካለትንም ቡድን አገኘ።

ጣህሪር አደባባይና ዓባይ
ስንት ሰዎች በካይሮ ያለው አደባባይ ከዓባይ ጋር ግንኙነት አለው ብለው ያምናሉ? እስቲ ጠጋ ብለን እንመርምረው፤ ጣህሪር አደባባይ የግብጽ ሕዝብ የነጻነት ጥሪ ነበር፤ በአሜሪካ አጋዥነት ተጭኖት የነበረውን አገዛዝ ለማውረድ ቆርጦ መነሣቱን የገለጸበት አደባባይ ነው፤ የጣህሪር አደባባይን ማእከል ባደረገ ቆራጥ ትግል አገዛዙን አንኮታኩቶ አወረደው፤ በሰላማዊና ሕጋዊ ምርጫ የግብጽ ሕዝብ አዲስ መንግሥትን መሠረተ፤  የእስልምና ወንድማማቾች የሚባለው ቡድን አሸናፊ ሆኖ መውጣቱን አሜሪካም ሆነ እሥራኤል በጸጋ የተቀበሉት አይመስልም፤ ስጋት አላቸው፤ ለግብጻውያን ከአገዛዙ ጋር የሚወርድ ሌላ ጭነት አለባቸው፤ አሜሪካ ለራስዋም ዓላማ ሆነ ለእሥራኤል ዓላማ በግብጽ ላይ የምታደርገውን ከባድ ጫና ማንሣት ከትግሉ ዓላማዎች አንዱ ነበር፤ አሜሪካንና እሥራኤልን ያሰጋው የለውጡ ዓላማ አገዛዙን መጣሉ ሳይሆን በእነሱ ጥቅም ላይ ያነጣጠረውን ክፍል ነበር፤ በጦር መሣሪያ በኩል ግብጽ የአሜሪካ ጥገኛ ነች፤ ቀደም ሲል የሶቭየት ኅብረት ጥገኛ ነበረች፤ በአሁን በአለው የጊዜው ትርምስ አሜሪካ ግብጽ አንዳታመልጠው ይፈልጋል፤ ስለዚህም ስጋት አለው።
ግብጽን ሰንጎ ለመያዝና ለማስጨነቅ ከዓባይ የበለጠ ኃይል የለም፤ ዓባይን ሰንጎ  ግብጽን ለማስጨነቅ ከኢትዮጵያ  የበለጠ  ምቹ  አገር  የለም፤ በተጨማሪም ኡጋንዳን፣  ኬንያንና ደቡብ ሱዳንን ከአሰለፈ ለአሜሪካ ሁኔታው ይበልጥ ይመቻቻል፤ ጫናው በግብጽ ላይ የጠነከረ ሊመስል ይችላል፤ አሜሪካ የግብጽን ወዳጅነት ለዘለቄታው ለማጣት ይፈልጋል? ለእኔ አይመስለኝም፤ አሜሪካ የአረቦችን ሁሉ ጠላትነት ይፈልጋል? ለእኔ አይመስለኝም፤ ታዲያ እስከምን ድረስ ነው አሜሪካ ግብጽን ለማስጨነቅ የሚፈልገው? ዋናው ጥያቄ ይህ ነው
ትልቁ የአስዋን ግድብ ሲሠራ የነበረውን ውዝግብና መካካድ ለማንሣት ይዳዳኛል፤ ግን ሰፊ በመሆኑ አልገባበትም፤ አንዳንድ ሁነቶችን ብቻ ልጥቀስ፡– የምዕራብ ኃይሎች በተለይም አሜሪካና ብሪታንያ ለግድቡ ሥራ አስተዋጽኦ ለማድረግ ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ ሀሳባቸውን ለወጡ፤ የሶቭየት ኅብረት አንድ ቢልዮን ተሩብ ያህል ዶላር ለማበደር ዝግጁ ሆነ፤ ግብጽም ብድሩን ለመክፈል እንድትችል በዓለም-አቀፍ ኩባንያ ይተዳደር የነበረውን የስዌዝ ቦይ ብሔራዊ ሀብትዋ አድርጋ አወጀች፤ ይህንን በመቃወም ብሪታንያ፣ ፈረንሳይና እሥራኤል ግብጽን ወረሩ፤ በተባበሩት መንግሥታት ግፊት (አሜሪካና የሶቭየት ኅብረት በተባበሩት መንግሥታት መድረክ ላይ በአንድ ላይ የቆሙበት ብርቅ ሁኔታ ነበር፤) ወረራቸውን አቁመው ከግብጽ ወጡ፤ በኋላ ነገሩ ሁሉ ተገለባብጦ ግብጽ ሶቭየት ኅብረትን ትታ የአሜሪካ ወዳጅ ሆነች!
አሜሪካ የሶርያን ሳይጨርስ፣ የኢራንን ሳይጀምር ከግብጽ ጋር ውዝግብ ቢጀምር ምን ጥቅም ያገኛል? ደግሞስ በዓባይ ጉዳይ በኢትዮጵያና በግብጽ ውዝግብ የሚያሸንፈው አሜሪካ መሆኑ ያጠራራል ወይ? አሜሪካ ሲያሸንፍ ግን ከኢትዮጵያና ከግብጽ አንዳቸው ይወድቃሉ፤ ወይም ይቆስላሉ፤ ሁለቱንም እኩል አያቅፋቸውም፤ ደርግ አሜሪካንን በማስቀየሙ በአለፉት ሃያ ዓመታት በኢትዮጵያ መሬትና በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ያስከተለው መዘዝ እያሰቃየን መሆኑን ልንረሳው አይገባንም
በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያና በግብጽ መሀከል ያለው ጉዳይ አህያ ላህያ ቢራገጥ ዓይነት አይመስለኝም።

“ከአንድነት ፓርቲ ጋር የሚደረገው ውህደት በግለሰቦች ደረጃ እንጂ በተቋሞቹ ውስጥ አልሞተም”

March 26/2014
አቶ አበባው መሐሪ
የመኢአድ ፕሬዝደንት

መጋቢት 11 ቀን 2004 ዓ.ም. በመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና በአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ መካከል የነበረው የቅድመ ፓርቲዎች ውህደት ሳይፈጸም ቀርቷል። ሁለቱም ፓርቲዎች አንዱ አንዱን እየከሰሱ ይገኛሉ።

በተለይ አንድነት በአመራሩ በኩል ከመድረክ ጋር ለመስራት ዝግጁ መሆኑን መግለፁ ለውዝግቡ መፈጠር በአይነተኛ ምክንያትነት ይጠቀሳል። መኢአድ በበኩሉ በብሔር ከተደራጁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ፍላጎት እንደሌለው ከበፊቶቹ አመራሮች እስከ አሁን ፓርቲውን ከሚመሩ አመራሮች ጭምር ወጥ አቋም ሲያንፀባርቁ ይሰተዋላል። ከዚህ መነሻነት ከአንድነት ፓርቲ ጋር ውህደት ለመፈጸም የጀመሩት ጉዞ በአንዳንድ የአንድነት አመራሮች ተጨናግፏል በማለት መግለጫ አውጥቷል። እኛም ይህን የውህደት ልዩነት ከግምት በመውሰድ የመኢአድ ፕሬዝደነት የሆኑትን አቶ አበባው መሐሪን አነጋግረናቸዋል።

ሰንደቅ፡- ድርድሩ ለምን በተፈለገው ፍጥነት አልሄደም? ለድርድሩስ አለመሳካት በመሰረታዊነት የሚያነሷቸው ነጥቦች ምንድን ናቸው?

አቶ አበባው፡-በመጀመሪያ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማሳወቅ የምፈልገው ድርድሩ አሁን በያዘው ቅርጽ ይሄዳል የሚል እምነት አልነበረንም። ሁሉም ነገር በቀና መንገድ ይጓዛል የሚል ጤናማ አመለካከት ይዘን ነበር ወደ ድርድሩ የገባነው። ሆኖም በእኛ ቀናነት ብቻ የሚሆን ነገር ባለመሆኑ ውህደቱ አለመሳካቱን ግንዛቤ ሊወሰድ ይገባል የሚል እምነት አለን።

ለድርድሩ አለመሳካት ቢያንስ ሶስት መሰረታዊ ነገሮች ማስቀመጥ ተገቢ ነው። አንደኛው፤ አንድነት ፓርቲ ከመድረክ ጋር በግንባር ለመስራት ፈቃድ የወሰደው ከምርጫ ቦርድ ነው። ይሄውም ከሌሎች ሶስት ፓርቲዎች ጋር በጋራ በምርጫ ሕጉ መሰረት ለመስራት አመልክተው ተፈቅዶላቸው እየሰሩ የሚገኙበት ሁኔታ ነው ያለው። ስለዚህም በመጀመሪያ ደረጃ ከመኢአድ ጋር ውህደት ለመፈጸም አንድነት ከመድረክ የግንባር አደረጃጀት መልቀቅ ይጠበቅበታል። አንድነት ከመድረክ መውጣት እስካልቻለ ድረስ ሕዝቡም እንደሚያውቀው ከመኢአድ ጋር መዋሃድ አይችልም። ምክንያቱም መኢአድ ከመድረክ ጋር ያለው ልዩነት ግልፅ በመሆኑ ነው። በእኛ በኩል በመጀመሪያ ከመድረክ ሙሉ ለሙሉ መውጣታችሁን የሚገልጽ መረጃ ስጡን የሚል ጥያቄ አቅርበናል። አያይዘንም ከእኛ ጋር ውህደት ከፈጸሙ፣ ከመድረክ ጋር በጋራ ሊሰሩ እንደማይችሉ አቋማችንን ግልጽ አድርገናል። እነሱም እንደሚገነዘቡት ውህደት ፈጽመን ወደ መድረክ በጋራ ልንሄድበት የምንችልበት አንዳችም ውለታ የለንም። ይህን መስመር ሊያጠራ የሚችል በአንድነት በኩል የቀረበ ማስረጃ የለም። ይህ በሆነበት ሁኔታ በጥድፊያ የቅድመ ፓርቲ ውህደት ፊርማ የምናኖርበት ሁኔታ ሊኖር እንደማይችል ገልጸንላቸዋል።

ሁለተኛው ነጥብ፤ በውህዱ ፓርቲ ውስጥ አስራ ዘጠኝ የሥራ አስፈፃሚ ቦታዎች ላይ እኩል ሃምሳ ሃምሳ ቦታ ይኑረን ብለናል። መኢአድ መዋቅራዊ አደረጃጀትና ስፋቱ የተሻለ መሆኑ ሁሉም ቢያውቀውም በመርህ ደረጃ ይህን ጥያቄ አቅርበናል። ሌላው፣ ለሊቀመንበሩ ቦታ ግልፅ መስፈርት ይውጣለት ለሚለውም ጥያቄ በምንም መልኩ መስፈርት ሊወጣ አይችልም የሚል ምላሽ ነው የተሰጠን። በአጠቃላይ ሲታይ የድርድሩ ነጥቦቹ በግልፅ ሳይቀመጡ እና ውይይት ሳይደረግባቸው እንፈራረም ነው የሚሉት።ይህን መሰል አካሄድ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች ውስጥ ከዚህ በፊት ብዙ ተሞክሮዎች ስላሉ አልተቀበልነውም። ተመሳሳይ ስህተትም ለመፈጸም ዝግጁ አይደለንም።

ሰንደቅ፡- በውህደቱ ላይ የጊዜ ጥያቄ ብቻ ነው ያላችሁ?

አቶ አበባው፡- የጊዜም የሕግም ጥያቄ ነው ያቀረብነው። ጊዜ ለምትለው በአንድነት በኩል እነአቶ ብሩ ቢያንስ የቅድመ ፓርቲው ፊርማ ለመጋቢት 18 ይሁን የሚል መቃወሚያ አቅርበው ነበር። ኢንጂነር ግዛቸው ፈጽሞ አይሆንም የሚል ምላሽ አቅርበው በግድ ለመጋቢት 11 ነው የሆነው። መሰረታዊ ነጥቡ ግን አንድነት በመድረክ ላይ የሚከተለው ግልፅ ያልሆነ አካሄድ ነው። የሚገርመው የተፈጠሩትን ችግሮች ለመመልከት ከሥራ አስፈፃሚዎች መካከል አቶ ካሳሁን አበባ፣ አቶ ሲራክ አጥናፉ እና አቶ ገለቱ ጀጀርሳ የደቡብ ቀጠና አስተባባሪን ልከን ከኢንጅነሩ ጋር ውይይት እንዲያርጉ አድርገናል። በውይይቱም ከስምምነት ለመድረስ የቻሉ ቢሆንም፣ ከተስማሙ በኋላ መኢአድ ድርድሩን አፈረሰው የሚል መግለጫ ማምሻውን ማውጣታቸው በጣም አሳዛኝ ኃላፊነት የጎደለው ተግባር ነው። በተለይ ይህን መሰል ጥድፊያ የሚያሳየው፣ ከጀርባቸው የተለየ ተንኮል መኖሩን ነው።

ሰንደቅ፡- ከእርስዎ መረዳት አንፃር፣ የአንድነት ፓርቲ አቀራረብ ስትራቴጂክ ወይንስ ስልታዊ ነበር?

አቶ አበባው፡-እየተፈጸመ ካለው ሁኔታ የተረዳሁት ሂደቱ በሙሉ የአንድነት ሥራ አስፈፃሚ ወይም የምክር ቤቱ አካሄድ አይደለም። የግለሰብ እርምጃ ነው ጎልቶ የወጣው። በግለሰቦች እይታ ድርድሩ የሞተ ነው የሚመስለው። በፓርቲዎቹ በኩል ግን የሞተ ነገር አለ፣ የሚል እምነት የለኝም። በተለይ የአንድነት ሥራ አስፈፃሚ እየሆኑ ያሉትን ነገሮች በጥልቀት ያወቃቸው አልመሰለኝም። የግለሰቦች ማፈግፈግ፣ መቁነጥነጥ ከተመለከትነው ግን የአንድነት አካሄድ ስልታዊ እንጂ ስትራቴጂካዊ አካሄድ አድርጎ ለመቀበል በጣም አስቸጋሪ ሁኔታ ነው ያለው።

ሰንደቅ፡- በሁለቱ ፓርቲዎች መካከል አደራዳሪዎች መኖራቸው ይታወቃል። አደራዳሪዎቹ ይህን ችግር ሊፈቱት አልቻሉም? በምንስ አግባብ ነው የአደራዳሪነት ሚና የወሰዱት?

አቶ አበባው፡- መታወቅ ያለበት እነዚህን አደራዳሪዎች ኢንጅነር ግዛቸው ናቸው መርጠው ያመጧቸው። ቤታችንን አንኳኩተው የገቡት እራሳቸው ናቸው። እኛ አልመረጥናቸውም። እናሸማግላችሁ ሲሉን ነው ያየናቸው። መልካም፣ ለማሸማገል ከሆነ ብለን ተቀበልናቸው። በሂደት ግን ነገሩ ሁሉ የተገላቢጦሽ ነው የሆነው። ይህን ስል ግን ሁሉንም ሽማግሌዎች ማለቴ አይደለም።
ሰንደቅ፡- መኢአድ ባልመረጣቸው ሽማግሌዎች ለመደራደር መዘጋጀቱ በየዋህነት የሚወሰድ ነው ወይንስ የፖለቲካ ስህተት መሆኑን ይቀበላሉ?

አቶ አበባው፡-በእኛ በኩል የነበረው፤ እነዚህ ሰዎች ሙሁራን ናቸው። ለሀገር አስበው ነው ከሚል ቀና መነሻ ነው የተቀበልነው። በጀርባ በኩል የሚመጣ ነገር አለ ብለን አላሰብንም። እየወቀስኩ አይደለም፣ መጡብን ብቻ ለማለት ነው። በቀና ልቦና ነገሮችን መውሰድ በእኔ እምነት የፖለቲካ ስህተት አይደለም።

ሰንደቅ፡- በሌሎች ባለድርሻ አካላት የሚቀርበው ውህደቱ ሀገር በቀል ሳይሆን ውጭ ባሉ አካላት የተፈበረከ በመሆኑ ነው፣ ለአለመስማማት የዳረጋቸውም ከውጪ የመጣ ስለሆነ ነው እየተባለ ነው። በዚህ ላይ የእርስዎ ምላሽ ምንድን ነው?

አቶ አበባው፡- ትክክል ነው። ሆኖም ውህደቱን ሕዝቡ ይፈልገዋል። ዋናው ነጥብ መታየት ያለበት ይህ ይመስለኛል። ነገር ግን ከሁኔታዎች መነሻነት ከተመለከትነው የውህደቱ ጥንስስ ከውጪ ተቀምሮ የመጣ ነው የሚለው ጥርጣሬ ሚዛን የሚደፋ ነው። ስትራቴጂው የተነደፈው ውጪ ነው። ሀገር ውስጥ ያሉት አስፈፃሚዎች ናቸው። በእውነተኛ ፍላጎት የመጣ የድርድር ሂደት ቢሆን ስህተት ማንም ይስራ ማንም በትዕግስት ውህደቱን መፈጸም እንጂ ይቋረጥ የሚል የተጣደፈ የአደባባይ ምላሽ አይሰጥም። በእኛ በኩል ውይይቱ ይቀጥል እያልን እየጠየቅን በር ዘግተውብን ጥለውን ባልሄዱ ነበር። ስለዚህ የውህደቱ ቅመራው ያለው ውጪ ሀገር ነው።

ሰንደቅ፡- ቅመራው ውጪ ነው ብለው የሚያምኑ ከሆነ፣ እንዴት በዚህ ሂደት ውስጥ ተሳታፊ ይሆናሉ?

አቶ አበባው፡- ይህን ነጥብ በትክክል መመልከት ተገቢ ነው። የአንድነት ሥራ አስፈፃሚ እና የምክር ቤት አባላት ሁኔታውን በጥልቀት ሳይመለከቱት በቀናነት በተቆርቋሪነት እየሰሩ ነው የሚገኙት። የቅመራው ባለቤቶች አንዳንድ ግለሰቦች ናቸው። መታወቅ ያለበት ከአንድነት ፓርቲ ጋር የሚደረገው ውህደት በግለሰቦች ደረጃ እንጂ በተቋም ደረጃ አልሞተም። በርግጠኛነት ሁለቱ ፓርቲዎች ይህን ስልታዊ ቅመራ በጋራ በመሆን እናከሽፈዋለን። ምክንያቱም ይህ አሁን እየተቀነቀነ ያለው አስተሳሰብ የግለሰቦች በመሆኑ ነው። እንዲሁም የአንድነት ሥራ አስፈፃሚ የምክር ቤት አባላት ፍላጎት እንዳልሆነ ስለምንረዳ ነው። 

ሰንደቅ፡- በእናንተ አባላት የሚቀርበው ቅሬታ፣ አንድነት የመኢአድን መዋቅር ጠቅልሎ በመውሰድ ራሱን የበለጠ ለማደራጀት የሚፈልግ ፓርቲ ነው የሚል ነው፤ በዚህ ነጥብ ላይ ምን አስተያየት አልዎት?

አቶ አበባው፡- አንድነት መዋቅር አለው፣ የለውም የሚለው ክርክር እንደተጠበቀ ሆኖ፣ መኢአድ ያለውን መዋቅር ሰጥቶም ቢሆን ለሕዝባችን አማራጭ ፓርቲ መሆን በጋራ እስከቻልን ድረስ ብዙ ችግር የለውም።

ሰንደቅ፡- ሌሎች ወገኖች በበኩላቸው ገዢው ፓርቲ ሁለቱ ፓርቲዎች እንዳይስማሙ ሰርጎ ገብቷል እያሉ ነው የሚገኙት። ይህን ሃሳብ ምን ያህል ይጋሩታል?

አቶ አበባው፡- እንዲህ እንደሚባል እኛም እንሰማለን። የሚገርመው እኛ የተስማማነው ነገር ሳይኖር ገዢው ፓርቲ ምኑን ነው የሚያፈርሰው። አንድነት ከመድረክ ሙሉ ለሙሉ መውጣት አለበት ለሚለው ጥያቄ፣ አንድነት እንጂ ገዢው ፓርቲ ምላሽ መስጠት ያለበት አልመሰለኝም። መጠራጠሩ ግን ክፋት የለውም፣ ተጨባጭ ለማድረግ ግን ብዙ መስራት ይፈልጋል።

ሰንደቅ፡- በተደጋጋሚ ግለሰቦች እያሉ ነው። እነዚህ ግለሰቦች ለምን በይፋ በማሳወቅ አትታገሏቸውም?

አቶ አበባው፡- ጋዜጠኛ እንዲህ ብሎ አይጠይቅም። ከዚህ በፊት የነበረውን ቅንጅት ማን እንዳፈረሰው ታውቃላችሁ። ለምሳሌ ብርቱካን በእስር በነበረችበት ጊዜ ብርቱካን የታሰረችው በራሷ ችግር እንጂ በፓርቲ አይደለም። አዲስ ሰው መሾም አለበት ያለው ማነው? ከዚህ በፊት አንድነትን ከመድረክ ጋር ለማዋሃድ ሽማግሌ የነበሩት ሰዎች እነማን ናቸው? ከዶክተር ነጋሶ ጋር ከስምምነት የደረስንበትን ሰነድ አልፈርምም ያለው ማን ነው? ለምንስ ተደራዳሪ የነበሩት እንዲነሱ ተፈለገ? ድርድሩ ከቆመበት መጀመር ሲገባው ለምን እንደአዲስ እንዲጀመር ተፈለገ? ከመድረክ ውጪ ሆነናል ተብሎ በአደባባይ ከተናገሩ በኋላ፤ መለስ ብሎ ጋዜጦችን ጠርቶ ከመድረክ ጋር እንሰራለን ማለት ምን ማለት ነው? የአንድነት ወጣት አመራሮች መድረክን በአደባባይ እየተቃወሙ፣ ግለሰቦች ግን ከመድረክ ጋር እንሰራለን ለምን ይላሉ? ስለዚሀም የአንድነት ሥራ አስፈፃሚ እና ምክር ቤት ይህን እውነት ፈትሾ የውህደቱን ሂደት እንደሚቀጥል ተስፋ አለኝ። ይህ የማይሆን ከሆነም እንደበፊቱ በትብብር ለመስራት ዝግጁ ነን።

mandag 24. mars 2014

ኢህአዴግ ባደባባይ የወደቀውን ፈተና “በጓሮ” አለፈ


ለግልጽነትና ለተጠያቂነት ብሎም ለህዝቦች ጥቅም ቅድሚያ እንደሚሰጥ ህግ ደንግጎ የተቋቋመው ዓለም ዓቀፋዊ ተቋም ኢህአዴግ ያቀረበውን የይግባኝ ማመልከቻ ተቀብሎ ማጽደቁ አነጋጋሪ ሆኗል። በ2009 ኢህአዴግን “ያወጣሁትን መስፈርት አታሟላም” በማለት እውቅና የከለከለው ይህ ተቋም፣ ኢህአዴግ በሚከሰስባቸው ዋና ጉዳዮች ለውጥ ሳያደርግ የራሱን ውሳኔ የገለበጠበት አካሄድ እየተመረመረ እንደሆነ የጎልጉል ምንጮች ጠቁመዋል።
የኢህአዴግን የእውቅና ይግባኝ ጥያቄ ተቀብሎ ያጸደቀው የተፈጥሮ ሃብትን በትክክለኛ መንገድ ለሕዝብ ጥቅም መዋሉን በመከታተል ለአገራት እውቅና የሚሰጠው The Extractive Industries Transparency Initiative (EITI) የሚባለው ዓለም ዓቀፋዊ ተቋም ነው። ተቋሙ ኢህአዴግ በ2009 አቅርቦት የነበረውን የእውቅና ጥያቄ ውድቅ ሲያደርግ የሰጠው ምክንያት “የመያዶች ህግ የተሰኘው” አዋጅ ተግባራዊ እንዳይሆንና በአገሪቱ የተተከሉት አፋኝ ህጎች እስካልተወገዱ ድረስ ማመልከቻው እንደማይታይ በማሳወቅ ነበር።
በ2009 ጠ/ሚኒስትር የነበሩት አቶ መለስ “መሰዋት” በስተቀር ኢህአዴግ አንዳችም ለውጥ ባላደረገበት ሁኔታ ባለፈው ረቡዕ መጋቢት 19፤2006 (March 19፤2014) ይኸው እውቅና ሰጪ ተቋም የራሱን ውሳኔ ቀልብሶ ለኢህአዴግ እውቅና መስጠቱ የብዙዎችን ቀልብ ስቧል። ከውሳኔው ቀናት በፊት በጓሮ የሚወጠን ድርጊት እንዳለ መረጃ ደርሶት የማሳሰቢያ ተቃውሞ ያሰራጨው ሂውማን ራይትስ ዎች የተሰኘውየሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት እንዳለው ከሆነ ከተገለበጠው ውሳኔ በስተጀርባ ሚስ ክሌር ሾርት ከፊት ረድፍ ተቀምጠዋል።
ማመልከቻው እንደገና እንዲታይና የቦርዱ የቀድሞ ውሳኔ እንዲገለብጥ እየተንቀሳቀሱ የሚገኙት የቀድሞ የእንግሊዝ ዓለምአቀፍ ትብብር ሚ/ር የሆኑት ክሌር ሾርት መሆናቸውን የድርጅቱ መግለጫው ይፋ አድርጓል። እኚህ ግለሰብ የአፍሪካ አምባገነኖችን በመደገፍ የሚታወቁ ሲሆን ይህ ከጥቅማቸው ጋር የተሳሰረው ግንኙነታቸው አሁንም ኢህአዴግን እንዲደግፉ እንዳደረጋቸው ይነገራል፡፡ እንዲሁም በሌሎች ኢህአዴግ ባቋቋማቸው ዓለምአቀፋዊነት ሽፋን በተላበሱ ድርጅቶች ውስጥ የአመራር አባል በመሆን ሚስ ሾርት እንደሚያገለግሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የእንግሊዝ ፓርላማ አባል በነበሩበት ወቅትም ያላወጡትን ወጪ አውጥቻለሁ በማለት በብዙ ሺዎች የሚገመት ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው ያዋሉ መሆናቸው በወቅቱ ዴይሊ ቴሌግራፍ ባወጣው መረጃ አጋልጦ ነበር፡፡ የተወሰነውን ገንዘብ የመለሱ ቢሆንም ጋዜጣው በወቅቱ ያወጣው መረጃ ግለሰቧ የሕዝብን ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው የተጠቀሙ “ሙሰኛ” መሆናቸውን ያስረዳል፡፡
ክሌር ሾርት
ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው እንደሚሉት ከሆነ ባለፈው ረቡዕ ኦስሎ፤ ኖርዌይ ላይ ውሳኔው በተላለፈበት ወቅት ሚስ ሾርት በግልጽ የኢህአዴግ ደጋፊ በመሆን ተጽዕኖ በማድረግ ወደ ውሳኔ እንዲደረስ ግፊት አድርገዋል፡፡ ግለሰቧ ባላቸው ኃላፊነት በመጠቀም (የEITI የቦርድ ኃላፊ ናቸው) እንዲህ ዓይነቱ ግልጽና ወገናዊነት የታየበት ድጋፍ በማድረግ ከድርጅቱ አሠራር ውጪ ውሳኔ እንዲሰጥ ማድረጋቸው ለወደፊት በሚቀርቡ ማመልከቻዎች ላይ ከፍተኛ የሆነ የአሠራር ችግር እንደሚያስከትል ካሁኑ እየተጠቆመ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ከማዕድን ኢንቨስትመንት ጋር በተያያዘ ማህበራዊ ቀውስ የደረሰባቸው አካባቢዎች እንዳሉ የሚታወቅ ነው። በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት አካባቢዎች መካከል በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን ባልጸዳ የሽያጭ ሂደት ሼኽ መሐመድ ሁሴን አላሙዲ የገዙት ሻኪሶ የወርቅ ማዕድን በህዝብ ላይ እያደረሰ ችግር የሚዘገንን ነው። በየጊዜው ግልጽ ባልሆነ የማስፋፊያ ውል የሚፈናቀሉና ከፋብሪካው በሚወጣው ዝቃጭ ለከፍተኛ ብክለት የተጋለጡ ዜጎች ድምጻቸውን ሲያሰሙ መታሰራቸው፣ መገረፋቸው፣ ለይስሙላ በተቋቋሙ ፍርድ ቤቶች የተፈረደባቸው እንዳሉ ታዛቢዎች ያስታውሳሉ።
በጋምቤላ ኢንቨስትመንት ህዝብን እየበላ እንደሆነ የሚጠቁሙት ክፍሎች “ኢንቨስትመንት በከፍተኛ ደረጃ የሚደገፍና የሚበረታታ ተግባር ቢሆንም፣ ኢህአዴግ ፍትሃዊ በሆነ ደረጃ መጠቀም፣ ማስተዳደር፣ መምራትና ኢንቨስትመንቱን ህዝብ “የኔ” ብሎ በመቀበል እንክብካቤ እንዲያደርግ የሚያስችል ስርዓት አለማበጀቱን እንደ ዋንኛ ችግር ያነሳሉ። ኢህአዴግን ያዘጋጀው ህወሃት በራሱ ሰዎች አማካይነት ከውጪ ሰዎች ጋር እየተሻረከ ለህዝብ ጥቅም ሊውል የሚገባውን ሃብት ወደ ውስን ቋት እንደሚያግዝ የሚገልጹት እነዚሁ ክፍሎች” ይህ ዓለም የሚያውቀውን፣ ራሳቸው ህወሃቶችም የማይክዱትን እውነት ነው ብለዋል። ዜጎች የአገራቸው ሃብት ተጠቃሚ ከመሆን ይልቅ አካባቢያቸው ባደላቸው የተፈጥሮ ሃብት ሳቢያ መከራ ሲደርስባቸው፣ ሲሰቃዩ፣ ሲገረፉና፣ ሲገደሉ ማየት በተለመደባት ኢትዮጵያ ውስጥ ለኢህአዴግ የማይገባውን ካባ መደረብ ውሎ አድሮ የሚጋለጥ ክፉ ተግባር እንደሆነም አመልክተዋል።
አነስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙና ኢህአዴግ “ልማታዊ” የሚላቸው ኢንቨስተሮች ሳይሆኑ በከፍተኛ ደረጃ የሚመደብ መዋዕለ ንዋይ የሚያፈሱ ባለሃብቶች ኢንቨስት የሚያደርጉበትን አገር ለመምረጥ የመጀመሪያው መለያቸው የEITI ድረገጽ የአባል አገራት ዝርዝር እንደሆነ ስለ አሰራሩ የሚያውቁ ይናገራሉ። ኢህአዴግም አስፈላጊውን የምዝገባና የማመልከቻ መስፈርት በማሟላት የተቋሙን እውቅና የጠየቀው በድርጅቱ ድረገጽ ላይ ለመመዝገብ ነበር። የሁለት ጊዜ ሙከራው ቢከሽፋም በመጨረሻ ተሳክቶለታል። ስኬቱንና የስኬቱን መንገድ፣ በተለይም የዳይሬክተሯ ክሌር ሾርት ጉዳይና የተዘጋውን ፋይል በማንሳት ውሳኔው የተገለበጠበት አካሄድ ኦስሎ በሚገኘው ሃያ የቦርድ አባላት ባሉበት ተቋም ውስጥም ግራ ያጋባቸው እንዳሉ መረጃዎች አሉ።
ኢህአዴግ አጓድለሃል ተብሎ የሚከሰስባቸውን የዴሞክራሲ ግባቶችና የሰው ልጆች የተፈጥሮ መብቶች፣ አንዲሆም አፋኝ የተባሉትን ህጎች አጠናክሮ ተግባር ላይ ባዋለበት ሁኔታ፣ የዚሁ የአፈናው ሰለባዎች በተለያዩ ማጎሪያዎች ውስጥ ሆነው ድምጻቸውን በሚያስተጋቡበት ወቅት፣ EITI ከተቋቋመበት ዓላማና “መሰረቴ” ከሚለው የግልጽነትና ተጠያቂነት መርህ በተጻራሪ ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው መልኩ ለኢህአዴግ የደረበው ብሉኮ ጉዳይ እየተመረመረ አንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። ጉዳዩን የሚከታተሉ “ግልጽነትና ተጠያቂነት በኦስሎ ተፈረደባቸው” ሲሉ ምጸት ሰጥተዋል፤ የክሌር ሾርትንም አካሄድ በEITI የህወሃት/ኢህአዴግ ተወካይ በማለት ተችተዋል። ይህንኑ ጉዳይ እመልክቶ ከሳምንት በፊት ለሪፖርተር አጭር መልስ የሰጡት የማዕድን ሚኒስትሩ EITI ውሳኔውን ያነሳል የሚል ጥርጣሬ እንዳለባቸው የሚያሳብቅባቸው መልስ ሰጥተው እንደነበር ይታወሳል።
በዚህ ጉዳይ ላይ ዳያስፖራው እንደሚገባው አለመንቀሳቀሱ እንደ ሽንፈትና አቅጣጫ መሳት እንደሚቆጠር ለጎልጉል አስተያየታቸውን የሰጡ ጠቁመዋል፡፡ ዳያስፖራው ከጥቃቅንና ስሜታዊ ጉዳዮች በማለፍ በከፍተኛና አገራዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት የማድረግ አመለካከቱን ማስፋት እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ አለበለዚያ ኢህአዴግ እንደዚህ ዓይነቱን አጋጣሚ በመጠቀም የራሱን ገጽታ በዓለምአቀፍ መድረኮች እየወለወለ በማቅረብ የሥልጣን ዘመኑን እንደሚያራዝም ጠቁመዋል፡፡

mandag 17. mars 2014

ኢትየጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ አንድ የኩዌት መንግስት ባለስልጣንን ልጅን ገደለች።

march 17/2014


ኢትጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ የኩዌት የህዝብ ፣ የወጣቶች እና የስፖርት ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ሃሙድ ፉሊታ ልጅ የሆነችውን የ19 ዓመት ወጣት ነው ደረቷን እና ሆድዋን በቢላ 4 ቦታ በመውጋት የገደለቻት ።

ኢትዮጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ ስሟ ያልተጠቀሰ ቢሆንም የ22 አመት እድሜ እንዳላት ግን ተዘግቧል። ኢትዮጵያዊቷ ግድያውን ከፈጸመች በኋላ ለፖሊስ እጇን እንደሰጠች ለማወቅ የተቻለ ሲሆን አቃቢ ህግም ጉዳዩን እንደያዘው ታውቋል።

በተያዘው አመት ብቻ 13 የኪዌት ዜጎች በቤት ሰራተኞቻቸው መገደላቸውም ተጠቁሟል። በኩዌት የውስጥ ጉዳይ ሚንስቴር የህዝብ ጉዳዩቸ እና የደህንነት መረጃ ዳይሬክተር እንዳሉትት በኪዌት 81 ሺህ ኢትዮጵያዊያ ን ሰራተኞቸ የሚገኙ ሲሆን 45 ሺህ የሚሆኑት በቤት ሰራተኝነት የሚተዳደሩ ናቸው። ዳይሬክተሩ አክለውም በሃገሪቱ ለሚገኙ ህገወጥ ኢትዮጵያውያንን የሚየስጠልሉ ዜጎች ህጋዊ እርምጃ እንመሚወሰድባቸው ተናግረዋል።

ኢትዮጵያዊያን የቤት ሰራተኞች በኩዌት ገብተው እንዳይሰሩ የታገደ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን አሁን ደግሞ የኪዌት አንድ የፓርላማ አባል በሃገሪቱ የሚገኙ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ከሃገር እንዲወጡ ፓርላማው እንዲወስን ጥያቄ አቅርቧል።

በዓለም ዓቀፍ የሴቶች ቀን ዝክር፤ በእህቶቻችን ኮርተናል! (ግንቦት 7)

March 17, 2014
Ginbot 7 weekly editorialለዘንድሮው ዓለም ዓቀፍ የሴቶች ቀን መታሰቢያ በአዲስ አበባ ከተማ በተደረገው የሩጫ ትዕይንት ላይ ወጣት ሴቶች ባሳዩት ልበ ሙሉነት ኮርተናል። የሩጫውን ትዕይንት አስታከው፣ በአብዛኛው የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እንደሆኑ የተነገረላቸው ወጣት ሴቶች ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለህሊና እስረኞች መፈታት እና ለሀገር አንድነት ድምፃቸውን ከፍ አድረገው ጮኸዋል፤ ዘምረዋል። እነዚህ ወጣት ሴቶች በሥርዓቱ ምን ያህል እንደተማረሩ በቃላትም በአካል ንቅናቄም አሳይተዋል። ዘረኛውና ፋሽስቱ ወያኔ ግን “ለምን ተቃወማችሁኝ” ብሎ አስሯቸዋል፤ ከፊሎቹም የደረሱበት አይታወቅም። በእህቶቻችን ቆራጥነት ኮርተናል፤ በወያኔ የፈሪ ዱላ ደግሞ ተቆጥተናል። በ1997 እና 98 “የወላጆቻችን ድምጽ ይከበር” ያሉ ሕፃናትን የጨፈጨፈው ወያኔ በ2006 ወጣት ሴቶችን ከማሰቃየት ይመለሳል ብለን አናምንም። ወያኔ እስካልተወገደ ድረስ የፈሪ ዱላው የማይቀር ነገር ነው።
የወንዶቹን ያህል የተዘገበ አይሁን እንጂ በክፉም በደጉም ሴቶች ያልተሳተፉበት የኢትዮጵያ ታሪክ የለም። የቅርብ ጊዜ ታሪካችንን እንኳን ብናይ በፋሽስት ወረራ ወቅት ኢትዮጵያዊያን ሴቶች በአርበኝነት ዘምተው አዋግተዋል፤ ተዋግተዋል። በተለያዩ ምክንያቶች መዝመት ያልቻሉት ደግሞ በውስጥ አርበኝነት ተሰልፈው የጠላት ምስጢሮች ለአርበኞች እንዲደርሱ በማድረግ ከፍተኛ ጀብዱዎችን ፈጽመዋል። ከፋሺስት ወረራ ወዲህ በነበሩ ዓመታት ውስጥም ለፍትህ እና ለነፃነት በተደረጉ ተጋድሎዎች ሴቶች ጉልህ ተሳትፎ ነበራቸው። በተማሪዎች ትግል ውስጥ ለምሳሌ፣ ወጣት ሴቶች በአመራር ደረጃ በመሳተፍ ትግሉን መርተዋል፤ የሕይወት መስዋዕትነት ጭምር ከፍለዋል። ከዚያ ወዲህም በነበሩት ዓመታት በኢሕአፓ እና ሌሎችም ድርጅቶች አመራርና አባልነት ተሳትፈው ከፍተኛ ተጋድሎ ያደረጉ ኢትዮጵያዊያን ሴቶች ነበሩን። በቅርቡም በምርጫ 97 እንቅስቃሴም የሴቶች በተለይም የወጣት ሴቶች ተሳትፎ ምን ያህል ጉልህ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነውና እናስታውሳለን። ለምርጫ ድምጽ መከበር ወጣት ሽብሬ ደሣለኝን ጨምሮ በርካታ ሴቶች ሕይወታቸውን ሰውተዋል፤ ከዚያ የበለጡት ደግሞ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። ዛሬም እንደ ርዕዮት ዓለሙ የመሳሰሉ ጀግኖች በወያኔ ወህኒ ቤቶች እየማቀቁ፤ በየእለቱ ሰቆቃ (ቶርቸር) እየተፈፀመባቸው መሆናቸው በሀዘንና በቁጭት እናስባቸዋለን።
በሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ አስፈላጊነት በመፈክር ደረጃ አንስተን የምንተወው ጉዳይ አይደለም። የሴቶች ተሳትፎ ያልታከለበት ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ግቡም አይመታም፤ ቢመታም ዋጋ የለውም።
ከጥቂት ዓመታት በፊት የተካሄዱትን የሰሜን አፍሪቃና የመካከለኛው ምሥራቅ አብዮቶችን በአንክሮ የተከታተለ ማንኛውም ሰው ከሚገረምባቸው ነገሮች አንዱ ሴቶች ያሳዩት ቆራጥነት እና ያካሄዱት ብስለት የተሞላው ትግል ነው። በቱኒዚያ የወጣቶች እንቅስቃሴ ውስጥ ወጣት ሴቶች ከመጀመሪያው ጀምሮ የአመራር ቦታ በመያዝ ተሳትፈዋል። በግብጽም የወጣት ሴቶች እልህ ከወንዶቹ በልጦ ታይቷል። አሁን በዩክሬን ውስጥ የምናየው ሀቅም ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው።
የሴቶች በሕዝባዊ አብዮቶች በስፋት መሳተፍ ከቁጥር ማብዛት እጅግ የላቀ መሠረታዊ ጠቀሜታዎች አሉት። ጥቂቶቹን እንደሚከተለው መዘርዘር ይቻላል።
1.ለሴቶች ያልተመቸ ሥርዓት ለማንም አይመችም። ለማኅበረሰብ በጠቅላላ የሚመች ሥርዓት መገንባት ማለት በቅድሚያ ለሴቶች የሚመች ሥርዓት መገንባት ማለት ነው። ይህ ሥርዓት ደግሞ እነሱ እራሳቸው እየተሳተፉበት፤ ከዚያም አልፎ እየመሩትም ነው መገንባት ያለበት።
2.ሴቶች ከወንዶች በላይ ታጋሾች ናቸው፤ ሲያመሩ ደግሞ በቀላሉ አይመለሱም ተብሎ ይታመናል። እናም የሴቶች በተቃውሞ ትግል ውስጥ በብዛት መሳተፍ ሥርዓቱ በሕዝቡ ምን ያህል እንደተጠላ ግልጽ አመላካች ነው።
3.የወጣት ሴቶች በድፍረት ለተቃውሞ አደባባይ መውጣት ወጣት ወንዶችን ያጀግናል። የወጣት ወንዶች መጀገን ደግሞ ወጣት ሴቶቹን ይበልጥ ያጀግናል። ወጣት ሴትና ወንዶች በእርስ በርስ አርዓያነት ይጀጋገናሉ። እናም ወጣት ሴቶች አምረው ተነሱ ማለት ሁሉም ወጣቶች ሁሉ አምረው ተነሱ ወደማለት ያመራል።
4.የእናቶች መቁረጥ አባቶችን ያነሳሳል፤ የእናትም የአባትም መነሳት ደግሞ መላው ቤተሰብ በሥርዓቱ ላይ እንዲነሳ ያደርገዋል። እናም እናቶች አመረሩ ማለት መላው ቤተሰብ አመረረ ማለት ይሆናል።
5.የሴቶች በትግል አመራር ቦታ ላይ መገኘት በተቃዋሚዎች መካከል ኅብረትን፣ መተሳሰብን ባጠቃላይም ቤተሰባዊ ስሜት ይፈጥራል።
6.ሴቶችና ወንዶች አብረው ሲቆሙ ነው የመተባበር ጥቅም በጉልህ የሚታየው!
የእህቶቻችን በድፍረት ድምፃችሁን ማሰማት ያለው ትርጉም ከድምፃችሁ ከፍታ እና ከቁጥራችሁ በላይ ነው። ዛሬ ጥቂት እንኳን ብትሆኑ ነገ ብዙዎቻችን አርዓያነታችሁን እንድንከተላችሁ ያደርገናል። እናም እህቶቻችን በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ባሳያችሁን ድፍረት ተበረታተናል። ኢትዮጵያ ብሩህ ራዕይ ያላት፤ ቆራጥነትን የተላበሱ ወጣቶች ያሏት መሆኑን አሳይታችናል። ይህ ትንሽ ጅምር የትልቅ ሕዝባዊ ማዕበል መንገድ አመላካች ነው።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ዘረኛውንንና አምባነኑን ወያኔ ከጫንቃችን ለማውረድ በምናደርገው ትግል የእህቶችና የእናቶች ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ ያውቃል፤ ስለሆነም ሴቶች ትግሉን በስፋት እንዲቀላቀሉ ጥሪ ያደርጋል። ሴቶችና ወንዶች፤ ወጣቶችና አረጋዊያን ሁላችንም የወያኔን ዘረኛ አገዛዝን እንዲያበቃ በጽናት እንታገል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

torsdag 13. mars 2014

የሴቶች ንቁ ተሳትፎ ጉሌህ ሚና ይኖረዋሌ።

         በአንድ ሃገር የፖሇቲካ ሇውጥ ሇማምጣት የህዝብ ሙለ ተሳትፎ  አስፈሊጊነቱ አጠያያቂ አይዯሇም። ከህብረተሰቡ ክፈሌ ዯግሞ የሴቶች ንቁ ተሳትፎ  ጉሌህ ሚና ይኖረዋሌ። በሃገራችንም ይህን ከጥንት እስካሁን በተግባር እያያየነው እንገኛሇን።የንግስት ሳባ፤ የንግስት እላኒ፤የእቴጌ ጣይቱ፤በአስራዘጠኝ ስሌሳዎቹ የፊውዲሌ ስርአት ግርሰሳ የነበረ የሴቶች ተሳትፎ በአጠቃሊይ ሴቶች  ሇሃገራችን  ያዯጉረትን ንቁ ተሳትፎ ያሳያሌ።በላሊ በኩሌ ዯግሞ በ አምባገነን ስርዓቶች በከፍተኛ ሁኔታ ከሚጠቁ የህብረተሰብ ክፍልች በአብዛኛው ሴቶች ናቸው።በአሁኑ ሰአትም በሃገራችን ያሇው ዘረኛ እና ጨቋኝ መንግስትንም በከፍተኛ ሁኔታ ከሚያስጠይቁት እና ከሚያስኮንኑት አንደይ ይኸው በሴቶች ሊይ የሚያዯርሰው ሌክ ያጣ ጥቃት ነው።ይህንንም እውነታ ሃገር በቀሌ እና የውጭ ሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች አያሳወቁ ይገኛለ። በተግባርም እያየነው ነው። ሇምሳላ ያህሌ በአገዛዙ መሌካም አስተዲዯር እጦት የተነሳ በተፈጠረ የኑሮ አስከፊነት ወዯ አረብ ሃገር እየተሰዯደ በባርነት የሚገዙ እና ወዯረከሰ ስራ የሚሰማሩበት ሁኔታ፤በሃገር ውስጥም ገና በሇጋ እድሜያቸው ጀምሮ ገሊቸውን ሸጠው ኑሮን ሇማሸነፍ መውጣታቸው፤በየእስር ቤቱ በአምባገነኑ መንግስት ወታዯሮች እና ፖሉሶች የሚዯርስባቸው የመዯፈር ጥቃት፤ ሇነጻነት እና ሇመብት በመቆማቸው እና በመጻፋቸው እነ ብርቱካን ሚዯቅሳ ርዩተአሇም አሰፋ አጠቃሊይ ሁኔታ ስንመሇከት በሃገራችን ያሇውን የሴቶች ጥቃት እና እንግሌት ጥሌቀቱን እና ስፋቱን እናይበታሇን።ሇዚህ እና በአጠቃሊይሇዝብ ችግሮች ተጠያቂ የሆነው ይህ ጸረህዝብ እና ጸረኢትዮጰያ መንግስት ይህንንም ሇማስተባበሌ  ዱሞክራሲ እና በሌማት ሇህዝብ ማጃጃያነት እንዯሚጠበቅበት የሴቶችን መብቷ አስከብራሇሁ አስከብሬያሇሁ እያሇ ከጽሁፍ ባሊሇፈ ሇማጃጃያነት እየተጠቀመበት ይገኛሌ።
         እነዚህን እና ላልችን ስንመሇከት በአንድ በኩሌ በቁርጠኝነት እና በብሌሃት የተካኑ ሴቶች እንዲሎት ከትንት ጀምሮ ያሇውታሪካችን እስካሁን እንዯቀጠሇ እንማርበታሇን።በላሊ በኩሌ የታሊሊቆቻችንን ፈሇግ በመከተሌ በአሁን ሰአት ያሇውን ችግር ትኩረት ሰትተን እንድናየው ያስገድዯናሌከሴቶች መብትም አሌፈን በአጠቃሊይ የሃገራችን እና የህዝባችንን ችግር ማሇትም ኢትዮጵያችን እንዯ ኢትዮጵያ እንድትቀጥሌ፤በህዝባችን እየተቀመረ ያሇውን የእርስ በእርስ ግችት፤የአንድ ዘር የበሊይነት፤አባቶቻችን ዯማቸውን እና ህይወታቸም የገበሩሇት መሬታቸን ሇባእዲን እጅግ በረከሰ ዋጋ መቸብቸብ አሌፎም ሇጎረቤት ሇፖሇቲካ ጥቅም ሲባሌ ብቻ ሇጎረቤት ሃገሮች አሳሌፎ መስጠት፤የህዝባችን የኑሮ ሰቆቃ፤የመናገር የመጻፍ መብት ማጣት በመገንዘብ ያሇውን ዘረኛ እና አምባገነን መንግስት እኩይ ሴራ በማወቅ እና ሇሇውጥ በሚዯረገው ትግሌ እንዯ ጥንቶቹ ሴቶች ከህብረተሰቡ ጎን በመቆም ሌንሳተፍበት ይገባሌ።ሃገራችን ኢትዮጵያ ከመቼውም ጊዜ በበሇጠ እርዲታ ያሻታሌ እና እኛ ሴቶችም ፈጥነን እንድረስሊት።ይህ ዯግሞ እናቶቻችን እና እህቶቻችን ሇሃገራችን የከፈለትን መስዋዕትነትሇመጠበቅ የጣለብንንም አዯራ እንዲንበሊ ይረዲናሌ።ሃገራችንንም ከገባችበት አዘቅት ያወጣሌናሌ።  
 ኢትዮጲያ በክብር ሇዘሊሇም ትኑር!!!  

tirsdag 11. mars 2014

“በዴሞክራሲ” ስም የሚደረግ የመሬት ነጠቃና የዘር ማጥፋት ወንጀል በኢትዮጵያ

“በዚሁ ከቀጠለ አገሪቷ ወደ እርስበርስ ግጭት ማምራቷ አይቀሬ ነው”
panelist
በአይነቱ የመጀመርያ የሆነ የውይይት መድረክ የካቲት 27 2006ዓም/March 6, 2014/ በኦስሎ፣ ኖርዌይ ከተማ ተደረገ። Frontline Club Oslo በተባለ ድርጅት አማካኝነት በኢትዮጵያ በዴሞክራሲ ስም እየተካሄደ ያለውን የመሬት ነጠቃ እና የዘር ማጥፋት ወንጀል በተመለከተ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸውን አካላት በመጥራት ሰፋ ያለ ውይይት ተደርጓል። በስብሰባውም ላይም ከውጭ ጉዳይና  ከሌሎች መስሪያ ቤቶች፣ ከዩኒቨርሲቲ፣ ከመንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ በኦስሎ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲሁም ለጉዳዩ ቅርበት ያላችው አካላት ተገኝተዋል።
ስብሰባውን የጠራው ድርጅት በመወከል ስብሰባውን በንግግር የከፈቱት ማርየስ ቮንዳርፈር እንደተናገሩት Fronline Club የተባለ ድርጅት በኦስሎ የተቋቋመው በያዝነው ዓመት ሲሆን አላማውም በዓለምአቀፍ ታዋቂ የፊልም እና የፎቶግራፍ ባለሙያዎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ እና ምሁራንን በመጋበዝ በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይቶች እና ዶክመንተሪ ፊልሞችን ማቅረብ መሆኑን ገልጸዋል።  የዓመቱ  ስራውንም የጀመረው በዚሁ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ እንደሆነ ተመልክቷል።
ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ በሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አያያዝ ዙሪያ ጠንካራ ነቀፋና ተቃውሞ ያልተለየው መሆኑ ይታወቃል። የዚህም ውይይት ዋና አላማ በሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ዙሪያ የሚደርሰውን ችግር ትኩረት ለመስጠትና ተጽዕኖ ለማድረግ የሚያስችሉ አካላትን ጠርቶ ማወያየት ነው። በመሆኑም በውይይቱ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሰፍንና የሰብዓዊ መብቶች እንዲከበሩ የምዕራባውያን መንግስታት በተለይም የኖርዌይ መንግስት ሚና ምን መሆን እንዳለበት በስፋት ትኩረት ተሰቶበታል። በውይይቱ ላይ አራት የተለያዩ አካላት ንግግር አድርገዋል።Abdulahi
የውይይቱ የመጀመሪያ ተናጋሪም አቶ አብዱላሂ ሁሴን ሲሆኑ እርሳቸውም የሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት ልዩ አማካሪና የኦጋዴን ቲቪ ቻናል ሃላፊ ሆነው ሰርተዋል። ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ሲሰሩ በነበሩበት ወቅት ያሰባሰቡትን መረጃ በቪድዮ የተደገፈ ዶክመንተሪ በዚህ ስብሰባ አቅርበዋል። የቀረበው ቪድዮ በክልሉ ፕሬዝዳንት እና በክልሉ ባለስልጣናት፣ ፖሊሶችና የጸጥታ አካላት መካከል የተደረጉ ምስጢራዊ ስብሰባዎችን አካቷል። በክልሉ እየተደረገ ያለውን ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ማሰርን፣ ማሰቃየትን፣ ግድያን እና በሴቶች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት እና ስቃይ ራሳቸው የጸጥታ ኃይሎች የሰጡትን ምስክርነት ዶክመንተሪው አካቷል። በመንግሥት ወታደሮችና ፖሊሶች አማካኝነት በክልሉ እየደረሰ ያለውን አሰቃቂ ወንጀሎች ዶክመንተሪው በማስረጃነት የሚያሳይ በመሆኑ በቀጣይነት ሄግ ለሚገኘው አለም አቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት እንደሚያቀርቡ አቶ አብዱላሂ አመልክተዋል።
በሶማሌ ክልል በሚሰሩበት ወቅት በተለያዩ ቦታዎች በህዝቡ ላይ እየተፈጸመ ያለውን ችግር የተመለከቱ መሆኑን ከመጥቀሳቸው በተጨማሪ በአሰቃቂ ሁኔታ የሚካሄደው የዘር ማጥፋት ወንጀል ትኩረት እንዳልተሰጠው ተናግረዋል። ዓለምአቀፉ ማህበረሰብም ሆነ አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ይህንን በመንግስት ባለስልጣናት እና የጸጥታ ኃይሎች እየደረሰ ያለውን የዘር ማጥፋት ወንጀል በተመለከተ በቂ መረጃ እንደሌላቸው አቶ አብዱላሂ አመልክተዋል። ይህ የሆነበትን ምክንያት ለማስረዳት ተናጋሪው ሁለት ነጥቦች አንስተዋል። በመጀመሪያ ደረጃ ኢህአዴግ ጋዜጠኞችንና ዓለምአቀፍ ገለልተኛ ድርጅቶች ወደ ክልሉ እንዳይንቀሳቀሱ በመከልከሉ ሲሆን ይህም ድርጊት በተጨባጭ በክልሉ እየደረሰ ያለው እውነታ እንዳይሰማ፣ እንዳይታይ አድርጎታል። በሁለተኛ ደረጃ ኢህአዴግ ምዕራባዊያንን በውሸት የማሳመኑን ስልት የተካነበት በመሆኑ እስካሁን በክልሉ የሚደርሰውን የዘር ማጥፋት ወንጀል በመሸፈኑ ተገቢውን ትኩረት እንዳያገኝ አድርጎታል ብለዋል። የሳቸውም አላማ ይህንን የሰበሰቡትን የቪዲዮ መረጃ ለዓለምአቀፉ ህብረተሰብ በማቅረብና በክልሉ የሚደርሰውን የዝር ማጥፋት ወንጀል በማስቆም ለዚህ ተጠያቂ የሚባሉ ባለስልጣናትና የጸጥታ ኃይሎች ለፍርድ እንዲቀርቡ ማድረግ መሆኑን ተናግረዋል።
በመቀጠል ንግግራቸውን ያደረጉት እውቁ የሰብአዊ መብት ተሟጋች እና ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዳይሬክተር የሆኑት የተከበሩ አቶ ኦባንግ ሜቶ ሲሆኑ የኖርዌይ ህዝብና መንግስት ለኢትዮጵያውያን ብሎም ለአጠቃላይ ሰብዓዊነት እያደረጉ ያለውን አስተዋጽዖ በማድነቅ ንግግራቸውን ጀምረዋል። በግጭትና በተለያዩ የፖለቲካ ቀውሶች ምክንያት በዓለማችን ተጠቂ ህዝቦች ካንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ የመሰደዱ ሁኔታ የተለመደ መሆኑን በማመልከት ብዙ ስደተኞች ወደ ኖርዌይ የሚመጡበት ምክንያት አገሪቷ ሃብታም እና የበለጸገች ስለሆነች ብቻ ሳይሆን የአገሪቱ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ እና ለሰብዓዊነት ክብር ቅድሚያ በመስጠቷ መሆኑን አቶ ኦባንግ አመልክተዋል።
Panelist2በኢትዮጵያ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና የመሬት ነጠቃ ሁኔታ በመጥቀስ የኖርዌይ መንግስትና እርዳታ ሰጪዎች ሊወስዱ የሚገባቸውን እርምጃ በንግግራቸው ጠቁመዋል። በመቀጠልም ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሃብት የሚያሳይ ምስል በማቅረብ ምን ያህል አገሪቱ በተፈጥሮ የታደለች መሆኑንና ያገሪቱ ዋና ችግር የመልካም አስተዳደር እጦት እንደሆን አስረድተዋል። በስልጣን ያለው አገዛዝ በህዝቡ ላይ የሚያደርሰው ጭቆና አላንስ ብሎ የአገሪቱን መሬት ለህንድ፣ ለቻይና እና ለሳውዲ ኢንቨስተሮች በርካሽ እየሸጠ ይገኛል። በዚህም ምክንያት ከሚሸጠው መሬት የሚፈናቀሉ ዜጎች በአስከፊ የድህነት ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ በመጥቀስ የሚያፈናቀሉት ዜጎች ህይወት በመሬቱ ላይ የተመረኮዘ በመሆኑ ኢህአዴግ በኢንቨስትመንት ስም የሚደርገው ድርጊት የዜጎችን ኑሮ አናግቷል። ምዕራባዊያን አገሮችም በተለይም የኖርዌይ መንግስት ይህንን አስከፊ የህዝቡን ስቃይ እና ችግር እያዩ እንዳላዩ በመሆን ለአምባገነናዊ መንግስት የሚያደርጉትን ድጋፍ እና ድጎማ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ ይገኛሉ። ይህም የምዕራባዊ መንግስታት ዕርዳታ ህዝቡ እራሱን በራሱ ከአምባገነናዊ አገዛዝ ነጻ እንዳያወጣና ለማውጣት የሚያደርገውን ጥረት ላይ ትልቅ እንቅፋት እንደሆኑበት አቶ ኦባንግ ተናግረዋል።
ይህ ሁኔታም በዚሁ ከቀጠለም አገሪቷ ወደ እርስ በርስ ግጭት የማምራት ሁኔታ አይቀሬ መሆኑን በማመልከት ምዕራባዊ አገሮች በተለይ የኖርዌይ መንግስት ይህ ከመሆኑ በፊት የህዝቡ ስቃይ እና እንግልት የሚቆምበትን መንገድ በማፈላለግ እና በኢትዮጵያ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲያብብ ትልቅ ሚና መጫወት እንዳልባቸው አቶ ኦባንግ አሳስበዋል።
በሶስተኛ ደረጃ ንግግራቸውን ያደረጉት ዮሃን ሂላን የተባሉ የማህበራዊ ምሁር ሲሆኑ በሰሜን እና በምስራቅ አፍሪቃ በልማት ዘረፍ የማማከር እና የምርምር ስራ እየሰሩ እንደሚገኙ ከመድረኩ ተጠቅሷል። ባሁን ወቅትም በርገን በሚገኘው በክርስትያን ኤይድ ኢንስቲትዩት ውስጥ እየሰሩ ሲሆን ይህም ኢንስቲትዩት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በትብብር እንደሚሰራ ታውቋል። እኝህ ምሁር ከኢህአዴግ ጋር ያላቸውን ቀረቤታ እና ለአምባገነናዊው መንግስት ያላቸውን አወንታዊ አስተያየት በሚያመለክት መልኩ ንግግር አድርገዋል። በስልጣን ላይ ያለው “መንግሥት” ከጎረቤት አገሮች አንጻር የተሻለ መረጋጋትና የኢኮኖሚ ዕድገት የሚታይበትን መሆኑን ገልጸዋል። ነገር ግን እኝህ ምሁር ባቀረቡት አስተያየት ላይ ከመድረኩም ሆነ ከተሳታፊዎች ትችት ተሰንዝሮባቸዋል። ከውይይቱ ተሳታፊዎች እንደተገለጸው እንደ ዮሃን ሂላን የመሰሉ ምሁር ነን ባይ ግለሰቦች የኢትዮጵያ ህዝብ በምን ሁኔታ እንዳለ የማያውቁና በተጨባጭ እውነታውን የማያሳይና የተሳሳቱ መረጃዎችን በመጠቀም የምርምር ውጤቶችን የሚያቀርቡ ምሁራን እንዳሉ የተጠቆመ ሲሆን በዚህም የተሳሳተ የምርምር ድምዳሜ ምክንያት ምዕራባውያን መንግስታት የተወላገደ የፖሊሲ አቅጣጫ እንዲከተሉ አድርጓል።
በመጨረሻም በኖርዌይ የሚገኙ ኢትዮጵያዊ ጥገኝነት ጠያቂወች ዙሪያ የሚያጠነጥን ዶክመንተሪ ቪድዮ ያቀረቡት አርቲስትና የሰብአዊ መብት ተማጋች የሆኑት ሶልቬይ ስይቨርሰን ናቸው። ይህንን ዓይነቱን ጥናት ለማድረግ ያነሳሳቸው ዋናው ምክንያት የኖርዌይ መንግስት እና የኢትዮጵያ “መንግስት” ስደተኞችን ለመመለስ ያደረጉትን ስምምነት አሳስቧቸው መሆኑን ተናግረዋል። በኖርዌይ የሚገኙ የኢትዮጵያውያን ስደተኞች በከፍተኛ ችግር ላይ እንደሚገኙ በመጥቀስ የኖርዌይ መንግስትም ተገቢውን ትኩረት በመስጠት የጉዳዩን ውስብስብነት እንዳልተመለከተው ጠቁመዋል። ያቀረቡትን ዶክመንተሪ ለሚመለከታቸው አካላት እንደሚያቀርቡና የተሻለ የጥገኝነት ፖሊሲ እንዲቀረጽ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
በመጨረሻም በተነሱ ጉዳዮች ዙሪያ አጭር ውይይት የተደረገ ሲሆን የተለያዩ አካላት ጥያቄና አሰተያየቶች ሰንዝረዋል። የስብሰባው አዘጋጆችም በጉዳዩ ዙሪያ ተከታታይ ውይይት እንደሚደረግ በመጠቆም የዕለቱን መረሃ ግብር አጠቃለዋል።
ከስብሰባው ጋር በተያያዘ የተቀናበረ ቪዲዮ ለመመልከት እዚህ ላይ ይጫኑ